ኮሚሽኑ ለ11 አትሌቶችና ለክለብ አሰልጣኝ የደመወዝ እርከንና የማዕረግ እድገት ሰጠ

58
አዲስ አበባ ሰኔ 8/2011 የአማራ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን በአትሌቲክስ ዘርፍ በሀገር ውስጥና በዓለም አቀፍ መድረኮች ከፍተኛ ውጤት ላስመዘገቡ 11 አትሌቶችና ለ አንድ የክለብ አሰልጣኝ የደመወዝ እርከንና የማዕረግ እድገት ሰጠ። ዛሬ የእርከንና የማዕረግ እድገት ለመስጠት በተዘጋጀ መርሀግብር ላይ የተገኙት የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ፕሬዚዳንት ኮሎኔል አትሌት ደራርቱ ቱሉ ኢትዮጵያ በዓለም አደባበይ ስሟ ጎልቶ እንዲነሳ የአትሌቶች ድርሻ ከፍተኛ ነው። አትሌቶች ባደረጉት ብርቱ ጥረት የኢትዮጵያ ስምና ክብር በዓለም አደባባይ ከፍ እንዲል በማድረግ ለአገራቸውና ለህዝባቸው ኩራት መሆናቸውን ተናግረዋል። “ሽልማቱም አትሌቶች በቀጣይ በሚሳተፉባቸው የውድድር መድረኮች ሁሉ የላቀ ውጤት እንዲያስመዘገቡ ብርታት ይሆናቸዋል” ብለዋል። የክልሉ ፖሊስ ኮሚሽን ኮሚሽነር አቶ አበረ አዳሙ በበኩላቸው የክልሉ ፖሊስ አትሌቲክስ ክለብ አትሌቶች ያስመዘገቡት ድል ለህዝባቸውና ለሀገራቸው ኩራት መሆኑን ነው የገለጹት። “የክለቡ አባላት ባለፉት አስር ዓመታት በሀገር ውስጥና በዓለም አቀፍ መድረኮች በተለያዩ ርቀቶች ተወዳድረው ባስመዘገቧቸው ድሎች የሀገሪቱ ሰንደቅ ዓላማ ከፍ ብሎ እንዲውለበለብ አድርገዋል” ብለዋል። በቀጣይም ክለቡ የክልላቸውንና የሀገራቸው ስም የሚያስጠሩ አትሌቶች መፍለቂያ እንዲሆን ኮሚሽኑ አስፈላጊው ሁሉ ድጋፍ እንደሚያደርግ አስረድተዋል። አሰልጣኙን ጨምሮ ለ12 አትሌቶች የደመወዝ እርከንና የማዕረግ እድገት ሽልማት መሰጠቱን የገለጹት ደግሞ የኮሚሽኑ የኮሙኒኬሽን ሚድያ ዋና መምሪያ ኃላፊ ረዳት ኮሚሽነር ሰኢድ አህመድ ናቸው። በሽልማቱም ሁለት አትሌቶች የደመወዝ እርከን፣ አስሩ ደግሞ ከምክትል ሳጂን እስከ ዋና ኢንስፔክተርነት የማዕረግ እድገት መሰጠቱ ተገልጿል። በሽልማቱም በለንደን ማራቶን 42 ኪሎ ሜትሩን በሁለት ሰዓት ከ30 ደቂቃ በመግባትና ክብረወሰን በመስበር ጭምር የግሉ ያደረገው አትሌት ሞስነት ገረመው ይገኝበታል። ከአትሌቶች በተጨማሪ በስራቸው የላቀ ውጤት ያስመዘገቡ ሰባት የማርሽ ባንድ አሰልጣኝ አባላትም የገንዘብና የምስክር ወረቀት ሽልማት ተበርክቶላቸዋል ። በአለም አደባባይ በለደን ማራቶን ሪከርድ በመስበር በቅርቡ ያሸነፈው አትሌት ሞስነት ገረመው እልህ አስጨራሽ ውድድሮችን በማድረግ ተደጋጋሚ ድሎች ማስመዝገብ መቻሉን ተናግሯል። በዚህም እስካሁን 37 የወርቅ ሜዳሊያዎችን ለራሱ፣ ለክልሉና ለሀገሩ ማስገኘቱን ጠቁሞ በአገኘው ውጤት በዛሬው ዕለት ከዋና ሳጅን ወደ ኢንስፔክተርነት ማዕረግ ማደጉንና በእዚህም ደስተኛ መሆኑን ገልጿል። "የተሰጠኝ የማዕረግ እድገት ከፍተኛ ኃላፊነት በመሆኑ በቀጣይ ጠንክሬ በመስራት የሀገሬ ሰንደቅ ዓላማ በዓለም አደባባይ ከፍ ብሎ እንዲውለበለብና ስሟ እንዲጠራ ይበልጥ አነሳስቶኛል" ብሏል። በመርሀግብሩላይየኢትዮጵያአትሌቲክስፌዴሬሽንፕሬዚዳንትኮሎኔልአትሌትደራርቱቱሉንጨምሮሌሎችየፌዴሬሽኑናየክልሉከፍተኛየሥራኃላፊዎችተገኝተዋል።    
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም