በጣና ሐይቅ ላይ ከተከሰተው የእንቦጭ አረም 85 በመቶ ተወግዷል

91

ባህር ዳር ግንቦት 28 / 2011 በጣና ሐይቅ ላይ ከተከሰተው የእንቦጭ አረም 85 በመቶ መወገዱን የአማራ ክልል የአካባቢ፣ የደን፣ የዱር እንስሳትና ጥበቃ ልማት ባለስልጣን አስታወቀ፡፡

46ኛው የዓለም የአካባቢ ቀን በዓል ምክንያት በማድረግ የእንቦጭ አረም ጉብኝትና የፓናል ውይይት ተካሄዷል፡፡

የባለስልጣኑ የጣና ሐይቅ ሥርዓተ ምህዳር ጥበቃ ዳይሬክተር አቶ መዝገቡ ዳኘው ለኢዜአ እንደገለጹ አረሙ የተወገደው የሰው ጉልበትና ማሽኖችን በመጠቀም ነው፡፡

በሥራውም ሐይቁን ከወረረው  3 ሺህ 197 ሄክታር ውስጥ 2 ሺህ 700 ሄክታር የሚጠጋው አረም ተወግዷል ብለዋል፡፡

አረሙ ሐይቁን በሚያዋስኑ ስድስት ወረዳዎች 22 ቀበሌዎች መከሰቱን ያመለከቱት ዳይሬክተሩ፤ በ14 ቀበሌዎች የተከሰተውን አረም በ164 ሺህ በላይ ሕዝብ ተሳትፎ መወገዱን ተናግረዋል፡፡

በማሽኖቹም 18 ሄክታር አረም መወገዱን አስታውቀዋል፡፡ 

ይሁን እንጂ በስምንት ቀበሌዎች የተከሰተው አረም  ወጣቶችን በማደራጀት ከመጋቢት ወር ጀምሮ እየተነሳ መሆኑን አስረድተዋል፡፡

ከአረሙ አስቸጋሪ ተፈጥሯዊ ባህሪ አንፃር አሁን በተከናወነው ሥራ በዚህ ዓመት የተከሰተውን እንዳይስፋፋና እንዳይራባ ከማድረግ ባለፈ በቀጣይ የሚሆነው መገመት እንደሚያዳግት ተናግረዋል፡፡

እምቦጭን ሙሉ በሙሉ ከሃይቁ ለማጥፋት ረጅም ጊዜ ይጠይቃል ያሉት ዳይሬክተሩ፤ አረሙን ለመከላከል የሰውን ጉልበት መጠቀም አማራጭ እንደሌለው አመልክተዋል፡፡

በተጨማሪም ማሽኖችን መጠቀምና ሌሎች ሥነ ህይወታዊ ዘዴዎች  ጥቅም ላይ እንደሚውሉ  ጠቅሰዋል፡፡

አረሙን ቀጣይነት ባለው መንገድ ለመከላከል የጣና ትረስት ፈንድ ተቋቁሞ ከ54 ሚሊዮን ብር በላይ መሰባሰቡንና ከዚህ ውስጥ ለዚህ ዓመት 23 ሚሊዮን ብር በጀት ተመድቦ እየተሰራበት ነው ብለዋል፡፡

በቀጣይም የአምስት ዓመት ስትራቴጂያዊ ዕቅድ ተይዞ በመሰራት ላይ እንደሚገኝም አቶ መዝገቡ ተናግረዋል፡፡

በአረሙን ለማስወገድ በተደረገው እንቅስቃሴ የጥራት መጓደልና የከፍተኛ አመራሩ ቁርጠኝነትና ድጋፍ ችግሮች መታየታቸውን ገልጸዋል፡፡

በሊቦ ከምከም ወረዳ ግብርና ጽህፈት ቤት አካባቢ ጥበቃ ቡድን መሪ አቶ ተካ ኃይሉ በበኩላቸው አረሙን ለመከላከል ባለፉት ሰባት ዓመታት ጥረት ቢደረግም፤የአረሙ ስርጭት ሲጨምር ቆይቷል ብለዋል፡፡

በዚህ ዓመትም በአራት ቀበሌዎች ውስጥ 880 ሄክታር መሬት ላይ ከተከሰተው አረም ውስጥ በ714 ሄክታር ላይ የነበረውን መጽዳቱን ገልጸዋል፡፡

በወል መሬት የተከሰተውን አረም ሙሉ በሙሉ ማንሳት ተችሏል ያሉት ቡድን መሪው፣ በዚህም አረሙ አበባ ሳያብብና ፍሬ አፍርቶ እንዳይባዛ ማድረግ ተችሏል ብለዋል፡፡

በሊቦ ከምከም ወረዳ የአግድ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር አለባቸው ገብሬ በበኩላቸው አረሙ በሐይቁ ዙሪያ ያለው የግጦሽ መሬት በመውረር ጉዳት ማድረሱን አመልክተው፣በዚህም ምክንያት ንፁህ ውሃ ለማግኘት ካለመቻላቸውም በላይ፤ ከዓሣ ማስገር ሥራ ውጭ መሆናቸውን አስታውቀዋል፡፡

አረሙ እንዳይስፋፋ የማረምና የማቃጠል ተግባር እያከናወኑ ቢሆንም፤ አረሙ ተመልሶ በመከሰት ችግር እንደሚፈጥር ገልጸዋል፡፡

የአረሙ ከተከሰተ ወዲህ የሐይቅ መጠን መቀነሱንና የሙቀት መጠንን መጨመሩን የተናገሩት ያሉት ደግሞ የቅርኝ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ዳኛቸው ምስጋን ናቸው፡፡

አረሙ ከሐምሌ እስከ ጥቅምት ወር ይስፋፋል ያሉት አርሶ አደሩ፣ መንግሥት ጠንካራና የማያቋርጥ እርምጃ እንዲወስድ ጠይቀዋል፡፡

የአግድ ቀበሌ ዋና አስተዳዳሪ አቶ አግማሴ መኳንንት በበኩላቸው አርሶ አደሩን በቡድን በማደራጀት አረሙን ለማጥፋት የሚያደርገው ጥረት ተስፋ አስቆራጭ ቢሆንም፣ ሥራውን ከማጠናከር ውጭ አማራጭ እንደሌለ አስታውቀዋል፡፡

ቀኑን ምክንያት በማድረግ በሊቦከምከም ወረዳ አግድና ቅርኝ ቀበሌዎች ጉብኝት ተደርጓል፡፡

በወረታ ከተማም የክልል፣ የዞንና የወረዳ አመራሮችና ባለሙያዎች እነዲሁም እንግዶች በተገኙበት ፓናል ውይይት ተካሄዷል፡፡


የዓለም የአካባቢ ቀን የተከበረው በኢትዮጵያ ለ26ኛ በአማራ ክልል ደግሞ ለ22ኛ ጊዜ ነው።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም