ፌስቲቫሉ የብሄር፣ ብሄረሰቦችና ሕዝቦችን ባህል በማስተዋወቅ ትስስርን ለማጠናከር ሚና ነበረው-ተሳታፊዎች

66

ሶዶ ግንቦት 27 /2011 ፌስቲቫሉ የብሄር፣ ብሄረሰቦችና ሕዝቦችን ባህል በማስተዋወቅ ሠላም፣አንድነትንና ትስስርን ለማጠናከር ሚና እንደነበረው ተሳታፊዎች ተናገሩ፡፡

ወላይታ ሶዶ የደቡብ ብሄሮች፣ ብሄረሰቦችና ሕዝቦች ክልል አራተኛውን የባህል ፌስቲቫል ላለፉት ሦስት ቀናት ስታስተናግድ ቆይታለች፡፡
ከኮንሶ ዞን ካራት ዙሪያ ወረዳ የመጡት አቶ ደምሳሽ ደጋኖ ፌስቲቫሉ መቀራረብን የፈጠረ፣ልዩነትን የፈታና አንድነትን ያጠናክሩበት እንዲሁም አንዱ ከሌላው ልምድ የቀሰሙበትና ዕምቅ ባህላቸውን ያስተዋወቁበት መሆኑን አስረድተዋል፡፡

በፌስቲቫሉ የታየዉ ኅብረ-ብሄራዊነት በሕዝቦች መካከል ጠባብነትንና ዘረኝነትን የሚዘሩ አካላት እንደማይሳካላቸው በቂ ማሳያ ነው ብለዋል፡፡

በሁሉም የአገሪቱ ክፍል የሚገኙ ብሄረሰቦችን በማሰባሰብ በየአካባቢው ያሉ ጸጋዎቻችንን በማጉላት አንድነታችንንና ትስስራችንን ለማጠናከር ልንሰራ ይገባል ነው ያሉት፡፡

ፌስቲቫሉ በባህላዊና ሃይማኖታዊ መሰረቶች የተሳሰረን ሕዝብ የጋራ ሥነ-ልቡና አመላካች ነው ያለችው ደግሞ ከካፋ ዞን የመጣችው ወይዘሪት ገሊላ ሃብተማሪያም ነች፡፡

ባህላዊ ዕሴቶቻችንና የቱሪስት መስህቦቻችንን ከማስተዋወቅና ከመጠቀም ረገድ የተቀናጀ ሥራ እንዳልተሰራም ገልጻለች፡፡

በትውልድ መካከል የተፈጠረዉ የዕውቀት ክፍተት ያመጣውን በመጤ ባህሎች የመበረዝ ዕድል ለማስወገድ ትዉልዱን ከታች ጀምሮ መቅረጽ፣ማስተማርና ማስገንዘብ ይጠበቃል ብላለች፡፡

ከመለያየትና መከፋፈል ዕይታ በመውጣት አገራዊ አንድነትን በጠንካራ መሠረት ለማቆም የሚጠበቅባትንም ለመወጣት ዝግጁ መሆኗንም አረጋግጣለች፡፡

ከሐዲያ ዞን የመጣችዉ ወጣት ካሰች ደሳለኝ በበኩሏ ፌስቲቫሉ እርስ በርስ የተማማሩበት፣የተዋወቁበት ፣"አብሮነታችንና ፍቅራችንን ያጠናከርንበት እንዲሁም በልዩነታችን መካከል ያለውን ውበት አይተንበታል" ስትል አስተያየቷን ሰጥታለች፡፡

እንደሰንሰለት የተሳሰረ እንደሸማ ጥበብ በኅብረ-ቀለማት ያገጠ ኢትዮጵያዊ ማንነታችንን ወዳጆቻችን ብቻ ሳይሆኑ ጠላቶቻችንንም ጠንቅቀው ያዉቁታል ያሉት ደግሞ የባህልና ቱሪዝም ሚኒስትር ዶክተር ሂሩት ካሳው ናቸው፡፡

ቀደምት አባቶች ከንጹህ አዕምሮ ያፈለቁትን የባህል ዕሴቶቻችንን ጠብቀዉ ለማቆየት ብዙ መስዋዕትነት ከፍለዋል ያሉት ሚኒስትሯ፣ ዘመኑ ከደረሰበት በተሻለ መልኩ ለሠላምና ለልማት እንዲሁም ለሃገር አንድነት ያላቸው ሚና ሳይበረዝ እንዲሸጋገር ኃላፊነታችንን መወጣት ይገባል ብለዋል፡፡

ሚኒስቴሩ ባህላዊ ዕሴቶች በሥርዓተ ትምህርት ውስጥ እንዲካተቱና ተገቢውን ድጋፍና ትኩረት እንዲያገኙም እንደሚሰራ አረጋግጠዋል፡፡

በምክትል ርዕሰ-መስተዳደር ማዕረግ የደቡብ ክልል የከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ቢሮ ኃላፊ አቶ ክፍሌ ገብረማሪያም  የባህል እሴቶች የይቅርታና የፍቅር እንዲሁም የአብሮነት ዕይታዎችን በመጠቀም ከመንደር ይልቅ፤ አገራዊ ሥነ-ልቡናን ለመገንባትና አንድነትን ለመፍጠር የሚጫወቱት ሚና ከፍተኛ መሆኑን ተናግረዋል ፡፡

የክልሉ መንግሥት ግጭቶችን ለመከላከል ባህላዊ የግጭት አፈታት ሥርዓቶችን ከዘመናዊ በማስተሳሰር  እንደሚሰራም ገልጸዋል፡፡

ባህሎች ሳይበረዙና ይዘታቸዉን ሳይለቁ ለቀጣይ ትዉልድ እንዲተላለፉ የማስተዋወቅ፣የማስተማርና የሕዝቦችን ትስስር ለማጠናከር ቅድሚያ መስጠቱን  ኃላፊው ተናግረዋል፡፡

በፌስቲቫሉ የክልሉ ብሄሮች፣ብሄረሰቦችና ህዝቦች ተወካዮች ባህላዊ ዕሴቶቻቸዉንና በክልሉ የሚገኙ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ደግሞ የምርምር ሥራዎቻቸዉን በዐውደ-ርዕይ መልክ አቅርበዋል፡፡

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም