የጋምቤላና የኦሮሚያ ክልል የህዝብ ለህዝብ መድረክ በመጪው ሰኞ በጋምቤላ ከተማ ሊካሄድ ነው

64

ግንቦት 9/ 2011 የጋምቤላና የኦሮሚያ ክልል የህዝብ ለህዝብ መድረክ በመጪው ሰኞ በጋምቤላ ከተማ እንደሚካሄድ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ጽህፋት ቤት አስታወቀ። 

የመስተዳድሩ ጽህፈት ቤትና የካቢኔ ጉዳዮች ኃላፊ አቶ ታደለ እሬሶ ዛሬ ለኢዜአ እንደገለጹት ግንቦት 12 ቀን 2011 ዓ.ም በሚካሄደው መድረክ ላይ የሁለቱ ክልሎች እርሳነ መስተዳድሮች አቶ ኡሞድ ኡጁሉ እና አቶ ሽማልስ አብዲሳን ጨምሮ ሌሎች ከፍተኛ የሥራ ኃፊዎች ይገኛሉ።

መድረኩ በሁለቱ ክልሎች መካከል ያለውን የቆየ ግንኙነትና የአብሮነት እሴቶች ይበልጥ ለማጎልበት ያለመ መሆኑንም አመልክተዋል።

ከዚህም በተጨማሪ መድረኩ የሁሉቱ ክልሎች ህዝቦች የአካቢያቸውን ሰላም ነቅተው በመጠበቅ ለጋራ ልማት ተጠቃሚነት በአንድነት ለመስራት ቃል ኪዳን የሚገቡበት መድረክ መሆኑንም ገልጸዋል።

አቶ ታደለ እንዳሉት መድረኩ በተለይም እንደ ሀገር የተጀመረውን ለውጥ ህዝቦች አንድነታቸውን በማጠናከር ወደ ፊት ለማራመድ ጭምር የጎላ ፋይዳ ይኖረዋል ።

ለአንድ ቀን በሚካሄደው በዚሁ መድረክ ከሁለቱ ክልሎች የተውጣጡ ከ350 በላይ የሀገር ሽማግሌች፣ አባገዳዎችና የሃይማኖት አባቶች ይሳተፋሉ ብለዋል አቶ ታደለ።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም