የቤኒሻንጉል ጉምዝ ሊግ እግር ኳስ ውድድር በኩርሙክ ወረዳ አሸናፊነት ተጠናቀቀ

59
አሶሳ ሚያዚያ 14 /  201 የቤኒሻንጉል ጉምዝ ሊግ ዓመታዊ እግር ኳስ ክለቦች ውድድር በኩርሙክ ወረዳ አሸናፊነት ትናንት ተጠናቀቀ፡፡ ከታህሳስ ጀምሮ በተካሄደው ውድድር 12 ክለቦች ተሳትፈዋል፡፡ በዓመቱ ውድድር ማጠቃለያ ለዋንጫ ው በተደረገ ጨዋታ ኩርሙክ መንጌ ወረዳን አንድ ለባዶ በማሸነፍ ዋንጫ ባለቤት ሆኗል። ባምባሲ ወረዳ ደግሞ ሸርቆሌ ወረዳንም አንድ ለባዶ በመርታት ሦስተኛ ሆኖ አጠናቋል። በውድድሩ ከአንደኛ እስከ ሦስተኛ ደረጃ ለወጡ ክለቦች ኮሚሽኑ ከ35 ሺህ እስከ 25 ሺህ ብር የሚደርስ የማበረታቻ ሽልማት ተሰጥቷል፡፡ ኮከብ እና ምስጉን ተጫዋቾች፣ አሰልጣኞች፣ ዳኞች እና ረዳት ዳኞችም ከ2 ሺህ 800 እስከ 1 ሺህ 500 ብር ተሸልመዋል፡፡ ለውድድሩ ስኬትና ድምቀት አስተዋጽኦ ያደረጉ ባለድርሻ አካላትም የእውቅና ሰርተፊኬት አግኝተዋል፡፡ ሽልማቱን የሰጡት የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ አሻድሊ ሐሰንና የክልሉ አመራሮች ናቸው፡፡ ርዕሰ መስተዳድሩ በዚሁ ወቅት እንደተናገሩት በህዝቦች መካከል ያለውን አንድነትና ወዳጅነት ስፖርትን ማጠናከር ይገባል፡፡ ውድድሩን ከ5 ሺህ የሚበልጡ የአሶሳ ከተማ ና አካባቢው ነዋሪዎች  መከታተላቸውን የክልሉ ስፖርት ኮሚሽን የህዝብ ግንኙነት ዳይሬክተር አቶ ትዕዛዙ ታዬ ለኢዜአ ገልጸዋል፡፡    
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም