የአማራና የትግራይ ህዝቦች ወደ ግጭት የሚገቡበት አንዳችም ምክንያት የለም - ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ

76

አዲስ አበባ መጋቢት 19/2011 ''ክፉና ደጉን በጋራ ያሳለፉት የአማራና የትግራይ ህዝቦች ወደ ግጭት የሚገቡበት አንዳችም ምክንያት የለም'' ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ ተናገሩ።

ጠቅላይ ሚኒስትሩ ክልሎች የማይመስላቸውን አካሄድ በግልጽ የመቃወም ልምምድ እያዳበሩ መሆኑንም ገልጸዋል።

ጠቅላይ ሚኒስትሩ ዛሬ ለአገር ውስጥና ለውጭ ጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ ፤ የአማራና የትግራይ ህዝቦች ዘመናትን በተሻገረ ታሪካቸው በርካታ ችግሮችን በጋራ ተጋፍጠው አልፈዋል።

የአስተዳደር ወሰንን በሚመለከት ሁለቱ ክልሎች የተለያዩ ጥያቄዎችን እንደሚያነሱ ገልጸው፤ ''ነገር ግን ይህ ጥያቄያቸው የሰውን ህይወት አልቀጠፈም ነው'' ያሉት።

በአንጻሩ በመሰል ጥያቄ ሶማሌና የኦሮሞ ወንድማማቾች እርስ በርስ የተገዳደሉበት አሳዛኝ ክስተት የቅርብ ጊዜ ታሪክ መሆኑን አስታውሰዋል።

''ይህ የሚያሳየው የአማራና የትግራይ ህዝቦችን የወሰን ጥያቄ የማይገድበው ጥልቅ ወዳጅነት እንዳለቸው ነው'' ብለዋል።

ሁለቱ ክልሎች በጋራ በመሆን ችግሮቻቸውን ከመፍታት ባለፈ በወሰኖቻቸው አካባቢ የሚኖሩ ህዝቦቻቸውን ኑሮ ለማሻሻል ቅድሚያ እንዲሰጡ አሳስበዋል።

በሌላ ዜና በኢትዮጰያ ውስጥ የክልል መንግስታት የማይመስላቸውን አካሄድ በግልጽ የመቃወም ልምድ እንዳልዳበረ ገልጸው፤ ''አሁን ያለው ፖለቲካዊ ለውጥ ይህን ልምምድ እንድናይ አድርጓል'' ብለዋል። 

ከዚህ አንጻር በትግራይ ክልል የሚገኙ ምሁራንም ሆኑ የመንግስት አካላት የማይመስላቸውን አካሄድ ሲቃወሙ የፌዴራል ስርዓቱ አቅም እንዳጣ ተደርጎ መወሰድ እንደሌለበት ተናግረዋል።

ይህ አይነቱ ልምምድ ከትግራይ ክልል ባለፈም በሌሎች ክልሎች እየዳበረ መሆኑንም ጠቁመዋል። 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም