በዴንማርክ የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና የሚካፈለው የኢትዮጵያ ልዑክ ማምሻውን ወደ ስፍራው ያቀናል

86

አዲስ አበባ መጋቢት 17/2011 በዴንማርክ አርሁስ ከተማ በመጪው እሁድ በሚካሄደው የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና የሚካፈለው የኢትዮጵያ ሉዑክ ዛሬ ምሽት ወደ ስፍራው ያቀናል።

በዚህ አገር አቋራጭ ውድድር የሚካፈሉ አትሌቶችና ሌሎች የቡድኑ አባላት ትናንት ምሽት በአዲስ አበባ አራራት ሆቴል ሽኝት ተደርጎላቸዋል።

የልዑካን ቡድኑን የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌደሬሽን ፕሬዚዳንት ኮለኔል ደራርቱ ቱሉ ስትመራ አቶ ዱቤ ጅሎ ደግሞ የቴክኒክ ቡድን መሪ ናቸው።

ሶስት የህክምና ቡድን አባላት፣ ዘጠኝ አሰልጣኞችና የፌዴሬሽን የስራ አስፈጻሚዎ ኮሚቴ አባላትም ወደ ስፍራው ያቀናሉ።

በዚህ ውድድር የሚካፈሉ አትሌቶች የካቲት 3 ቀን 2011 ዓ.ም በተካሄደው የጃንሜዳ ኢንተርናሽል አገር አቋራጭ ውድድር የተመረጡ ናቸው።

የተመረጡት አትሌቶች ከየካቲት 6 ቀን 2011 ዓ.ም ጀምሮ በአዲስ አበባ አራራት ሆቴል ከትመው ልምምዳቸውን ሲሰሩ ቆይተዋል።

የፌደሬሽኑ ፕሬዚዳንት ኮለኔል ደራርቱ ቱሉ በሽኝቱ ላይ ባደረገችው ንግግር አትሌቶች ለውድድሩ በቂ ጊዜ በመስጠትና አስፈላጊውን ነገር ሁሉ በማሟላት በቂ ስልጠና አግኝተዋል።

ከተመረጡት አትሌቶች ብዙዎቹ በእንዲህ አይነት ውድድር ልምድ የሌላቸው ቢሆንም ጠንካራ አትሌቶች በመሆናቸው ጥሩ ውጤት ይመጣል የሚል እምነት እንዳላትም ነው የተናገረቸው።

ከቡድኑ አሰልጠኞች መካከል ዋና ሱፐር ኢንተዳንት ሁሴን ሽቦ ለዚህ ሻምፒዮና በቂ የልምምድ ጊዜ እንደነበራቸና በልምምድ ወቅትም ፌዴሬሽኑ አስፈላጊውን ሁሉ ድጋፍ ማድረጉን ገልጸዋል።

አትሌቶችም ባስተፋለፉት መልክት ጥሩ ልምምድ እንዳደረጉና ለአገራቸው የቻሉትን ሁሉ በማድረግ ድል ለማስመዝገብ መዘጋጀታቸውን ገልጸዋል።

ወደ ዴንማርክ የሚያመራው የኢትዮጵያ ልኡክ አጠቃላይ 46 አባላትን የያዘ ሲሆን ከእነዚህ መካከል 28ቱ አትሌቶች ናቸው።

ለ43ኛ ጊዜ የሚካሄደው የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና በአዋቂ ወንዶችና ሴቶች የ10 ኪሎ ሜትር፣ በወጣት ወንዶች 8 ኪሎ ሜትር፣ በወጣት ሴት 6 ኪሎ ሜርትርና በ8 ኪሎ ሜትር ድብልቅ የዱላ ቅብብል የሚካሄድ ሲሆን ኢትዮጵያ በሁሉም ርቀቶች ላይ የምትካፈል ይሆናል።

የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና ከ1965 ዓ.ም ጀምሮ በተለያዩ ሀገራት እየተካሄደ የሚገኝ ውድድር ሲሆን ኢትዮጵያ ደግሞ ከ1973 ዓ.ም ጀምሮ በዚህ ሻምፒዮና እየተካፈለች ትገኛለች።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም