ኢትዮ-ቴሌኮም ማርች 8ን አስመልክቶ 70 ሺህ የሞባይል ቀፎዎችን ለሴቶች በስጦታ ያበረክታል

80

አዲስ አበባ የካቲት 22/2011 ኢትዮ-ቴሌኮም ዓለም ዓቀፍ የሴቶች ቀን /ማርች 8/ን በማስመልከት 70 ሺህ የሞባይል ቀፎዎችን ከሲም ካርድና ከአየር ሠዓት ጋር ለሴቶች በስጦታ ሊያበረክት ነው።

ኩባንያው ስጦታውን ከመጋቢት 1 ቀን 2011 ዓ.ም. ጀምሮ በ846 ወረዳዎች ለሚገኙና የመግዛት ዓቅም ለሌላቸው ሴቶች ከሲም ካርድና ከ15 ብር የአየር ሠዓት ጋር ለመስጠት ዝግጅቱን አጠናቋል።

ስጦታውን ለማበርከት እንደ መነሻ የተወሰደው በዓለም ላይ ዝቅተኛና መካከለኛ ገቢ ባላቸው አገራት ሴት የሞባይል ተጠቃሚዎች ቁጥር ከወንዶች ጋር በንፅፅር ሲታይ ዝቅተኛ መሆኑ እንደሆነ ቴሌኮሙ አስታውቋል።

ከቅድመ መረጃ ጥቆማዎች መረዳት እንደሚቻለው በኢትዮጵያም የሞባይል ተጠቀሚ ሴቶች ቁጥር ከወንዶች ያንሳል።

የኢትዮ-ቴሌኮም ኤክስኪዩቲቭ ዳይሬክተር ወይዘሪት ጨረር አክሊሉ ለኢዜአ እንደገለጹት ሴቶችን የሞባይል አገልግሎት ተጠቃሚ ማድረግ የመረጃ፣ የማህበራዊና የኢኮኖሚ አገልግሎት ጥቅሞችን ያስገኛል።

በመሆኑም መግዛት የሚፈልጉ ነገር ግን ገቢያቸው አነስተኛ የሆነና ቀደም ሲል የሞባይል አገልግሎት ተጠቃሚ ያልሆኑ ሴቶችን በወረዳና በቀበሌ አማካኝነት በመምረጥ 70 ሺህ የሞባይል ቀፎዎችን ከሲም ካርድ ጋር በስጦታ ሊያበረክት መሆኑን ገልፀዋል።

ስጦታው የሞባይል አገልግሎት ተጠቃሚነት ከፆታ አንፃር ያለውን ልዩነት ለመቀነስና ሴቶችን ከዲጂታሉ ዓለም ጋር በማገናኘት ማህበራዊ ኃላፊነታቸውን እንዲወጡ ለማበረታታት መሆኑንም ዳይሬክተሯ ተናግረዋል።

በአገሪቱ የሚደረገውን ለውጥ ለማገዝ ብሎም ለመሰል ተቋማት አርአያ ለመሆን የበኩሉን ድርሻ ለመወጣት በማሰብ እንደሆነም አክለዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም