በዩኒቨርሲቲዎች ሠላማዊ የመማር ማስተማር ሂደቱ ተጠናክሮ ቀጥሏል

94

አዲስ አበባ የካቲት 14/2011 በሁሉም የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ሠላማዊ የመማር ማስተማር ሂደት ተጠናክሮ መቀጠሉን የሳይንስና የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ሚኒስቴር ገለጸ።

ሚኒስትሯ ፕሮፌሰር ሂሩት ወልደማርያም ለኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት እንደተናገሩት፤ በአሁኑ ወቅት በሁሉም ዩኒቨርሲቲዎች ሠላማዊው የመማር ማስተማር ሂደቱ ተጠናክሮ ቀጥሏል።

ከዚህ ቀደም ችግሮች ይስተዋሉባቸው የነበሩ ዩኒቨርሲቲዎች ያሉባቸውን ችግሮች አመራሮቻቸው የተለያዩ እርምጃዎችን በመውሰድ ለመፍታት ተሞክሯል ብለዋል።

ተማሪዎችም የእረፍት ጊዜ እንዲወስዱ በማድረግም ችግሮቹን ለማርገብ መሰራቱን ገልጸው፤ ሠላሙን ዘላቂ ለማድረግም የተማሪዎች አመለካከት ላይ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል።

ተማሪዎቹን ሊያነቃቁ የሚችሉ ንግግሮች እንዲሁም የተለያዩ ውይይቶችም በተለይም ከታዋቂ ግለሰቦች ጋር በሁሉም ዩኒቨርሲቲዎች እየተደረጉ መሆኑን ጠቁመዋል።

ጎን ለጎንም በአመለካከተ ላይ አዎንታዊ ለውጥ ሊያመጡ የሚችሉ ድራማና ሌሎች የጥበብ ሥራዎችም በስፋት እየተሰሩ መሆኑን ገልጸዋል።

ተማሪዎች ከኅብረተሰቡ ጋር ያላቸውን ግንኙነት እንዲያጠናክሩ ለማድረግም የበጎ አድራጎት ሥራ ላይ ተሳታፊ እንዲሆኑም መደረጉን ሚኒስትሯ አስረድተዋል።

ይህም ደግሞ ተማሪዎች ዓላማቸውን በደንብ አጥብቀው እንዲይዙ በማድረግ በየትኛውም ኃይል ተጠልፈው እንዳይወድቁ ለማድረግ ሚናው የጎላ መሆኑን ተናግረዋል።

በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ 45 የመንግሥት ዩኒቨርሲቲዎች ይገኛሉ።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም