ፍርድ ቤቱ የዋና ሳጂን እቴነሽ አረፋይኔን የዋስትና ጥያቄ ውድቅ አደረገ

87

አዲስ አበባ  የካቲት 5/2011 የፌዴራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት የዋና ሳጂን እቴነሽ አረፋይኔን የዋስትና ጥያቄ ውድቅ አደረገ።

ዋና ሳጂን እቴነሽ አረፋይኔ የእስረኞችን ጥፍር የመንቀልና ሌሎች የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችን አድርሰዋል በሚል 11 ክሶች ተመስርተውባቸዋል።

የቀድሞ የፌዴራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ አባል የነበሩት ዋና ሳጅን እቴነሽ አረፋይኔ በሽብር ወንጀል ተፈርጀው ታስረው በነበሩ የኦነግና የአርበኞች ግንቦት ሰባት አባላት ላይ ሽንት በመሽናት፣ ጥፍር በመንቀልና በሌሎችም ዘግናኝ በተባሉ የወንጀል ድርጊቶች ተጠርጥረው ነው በቁጥጥር ስር የዋሉት።

ተከሳሿ በተለምዶ ማዕከላዊ ይባል በነበረው የፌዴራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ቢሮ የምርመራ ቡድን መርማሪ ሆነው ሲሰሩ ካልተያዙ ግብረ አበሮቻቸው ጋር በመሆን በሽብር ተግባር ወንጀል ተፈርጀው በታሰሩ ዜጎች ላይ ፈጽመዋል የተባለውን የወንጀል ድርጊት አቃቤ ሕግ ለፌዴራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት አቅርቦ የነበረው ክስ ያስረዳል።

ዛሬ የዋና ሳጂን እቴነሽ የዋስትና ጥያቄ ላይ ትዕዛዝ ለመስጠት ቀጠሮ ይዞ የነበረው የፌዴራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት 1ኛ ወንጀል ችሎት የተከሳሿን የዋስትና ጥያቄ ሳይቀበለው ቀርቷል።

ተከሳሿ የዋስትና መብታቸው እንዲከበር፣ ካልሆነም አዲስ አበባ ማረሚያ ቤት እንዲቆዩና ጉዳያቸውን እንዲከታተሉ፤ እንዲሁም ጡት የምትጠባ ሕፃን ልጃቸውን በተመለከተ ፍርድ ቤቱ ትእዛዘ እንዲሰጥ ጠይቀው ነበር።

ተከሳሿ በመገናኛ ብዙሃን በቀረበብኝ ፕሮግራም ሳቢያ ወደ ቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ለመውረድ ለደሕንነቴ ስለምሰጋ በአዲስ አበባ ማረሚያ ቤት እንደቆይ ይፈቀድልኝ ሲሉ ጠይቀዋል።

ፍርድ ቤቱም ተከሳሿ ከቀረበባቸው ክስ ውስጥ በተለይም 1ኛ እና 2ኛ ክስ አለአግባብ ስልጣንን በመጠቀም የሙስና ወንጀል በመሆኑና ይህም እስከ 10 ዓመት እንደሚያስፈርድ በመጥቀስ የዋስትና ጥያቄው ተቀባይነት አለማግኝቱን ገልጿል።

በተጨማሪም አንድ ተጠርጣሪ በአዲስ አበባ ማረሚያ ቤት ሊቆይ የሚችለው በጊዜ ቀጠሮ ምርመራ ላይ ክስ እስኪመሰረት በመሆኑ ወደ ቂሊንጦ ማረሚያ ቤት እንዲወሰዱና ጉዳይቸውን በዛው ሆነው እንዲከታተሉ ትዕዛዝ ሰጥቷል።

ነገር ግን በደህንነታቸው ላይ ምንም አይነት ስጋት እንዳይኖራቸው፣ ማረሚያ ቤቱም ሕገ-መንግስታዊ መብታቸውን እንዲያስከብር በማለት ነው ፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ የሰጠው።

በተጨማሪም ዋና ሳጂን እቴነሽ ከቤተሰቦቻቸው ጋር መክረው ልጃቸው አብራቸው እንድትሆን ከፈለጉም ማረሚያ ቤቱ እንዲቀበላቸው አዟል።

በመጨረሻም ፍርድ ቤቱ የዋና ሳጂን እቴነሽ አረፋይኔን የክስ መቃወሚያ ለመቀበል ለየካቲት 13 ቀን 2011 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም