ኢትዮጵያውያን ኢንተርናሽናል ዳኞች ከፊፋ የተላከላቸውን ባጅ ተቀብለዋል

68

አዲስ አበባ የካቲት 5/2011 ኢትዮጵያውያን ኢንተርናሽናል ዳኞች ከዓለም አቀፉ እግር ኳስ ማህበር (ፊፋ) የተላከላቸውን የ2018/19 የፊፋ ባጅ ተቀብለዋል።

ዳኞቹ የፊፋን ባጅ የተቀበሉት ትናንት በኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን የመሰብሰቢያ አዳራሽ በተካሄደ ስነ ስርአት እንደሆነ ፌዴሬሽኑ ገልጿል።

ሰባት ኢንተርናሽናል ዋና ዳኞች እንዲሁም ሰባት ኢንተርናሽናል ረዳት ዳኞች በድምሩ 14 ወንድ ኢንተርናሽናል ዳኞች እና አራት ኢንተርናሽናል ዋና ዳኞች እንዲሁም አራት ኢንተርናሽናል ረዳት ዳኞች በድምሩ ስምንት ሴት ኢንተርናሽናል ዳኞች በአጠቃላይ 22 ዳኞች ባጁ ተበርክቶላቸዋል።

ባምላክ ተሰማ፣በላይ ታደሰ፣ለሚ ንጉሴ፣ቴዎድሮስ ምትኩ ባጁን ካገኙት የወንድ ኢንተርናሽናል ዋና ዳኞች መካከል የሚጠቀሱ ሲሆን ሊዲያ ታፈሰና አስናቀች ገብሬ ባጁን ካገኙት የሴት ኢንተርናሽናል ዋና ዳኞች መካከል ይገኙበታል።

ኢንተርናሽናል ዳኞቹ ከኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አባልና የዳኞች ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ ዮሴፍ ተስፋዬና የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አባል አቶ አሊሚራ መሃመድ እጅ የፊፋ ባጃቸውን ተቀብለዋል።

የ2018/19 የፊፋ ባጅ ዳኞቹ እ.አ.አ በ2019 ፊፋ በሚያካሄዳቸው ዓለም አቀፍ የእግር ኳስ ውድድሮች ላይ እንዲመሩ የሚያስችላቸው ነው።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም