በድሬደዋ ወጣቶች የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎቻቸው ምላሽ እንዲሰጣቸው ጠየቁ

56

ድሬዳዋ ጥር 17/2011 የዓመታት የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎቻቸው በአፋጣኝ ምላሽ እንዲሰጣቸው በድሬደዋ ወጣቶች ባካሄዱት ሰልፍ ጠየቁ፡፡

ወጣቶቹ በተለያዩ የከተማው አስተዳደር አካባቢዎች በመዘዋወር ባካሄዱት ሰልፍ ጥያቄያቸውን  ባሰሟቸው መፈክሮች  አስተጋብተዋል፡፡

በዚህም ድሬዳዋ ሁሉም ብሔሮችና ብሔረሰቦች በፍቅር በአንድነትና በእኩልነት የሚኖሩባትን መሆኗን ጠቅሰው አብዛኛውን ወጣትና ህዝብ ያገለለ የመንግስት መዋቅርና አሰራር ሊፈርስ እንደሚገባ አመልክተዋል፡፡

በተግባር ላይ ያለው የፖለቲካ የስልጣን ክፍፍልና አሰራር የአብዛኛውን ህዝብና ወጣት ከልማት ተጠቃሚነት ያገለለ መሆኑን ወጣቶቹ ገልጸዋል፡፡

መዋቅሩ ወጣቱን ለከፋ የመልካም አስተዳደር ችግር የዳረገው በመሆኑ በፍጥነት እንዲቀየር ጠይቀዋል፡፡

በሰልፉ የተካፈለው ወጣት ሰለሞን መክብብ  በሰጠው አስተያየት የአስተዳደሩ ከንቲባ ወጣቶችን ለማናገር የያዙትን ቀጠሮ መሰረዛቸው በወጣቶቹ ዘንድ ቁጣ መቀስቀሱን ተናግራል፡፡

" እኛ ሁሉም ወጣቶች የሚሳተፉበት ውይይት ነው የምንፈልገው ፤ የወጣቶች ወኪል እየተባለ አዳራሽ የሚሰበሰበው እኛን ስለማይወክሉ የውክልና ውይይት አንፈልግም" ብሏል፡፡

" አንድም ባለስልጣን ቀርቦ  ያናገረን የለም፤ ከተማዋ መሪ የላትም፤ የፌደራል መንግስት በአስቸኳይ ጣልቃ ገብቶ ለጥያቄዎቻችን ምላሽ እንዲሰጠን እንፈልጋለን"  ያለው ደግሞ ሌላው የሰልፉ ተካፋይ ወጣት ሲሳይ አየለ ነው፡፡

በሁሉም  መስክ አድሏዊነት የሌለው ፍትሃዊ ተጠቃሚነት እንዲኖር ጠይቋል፡፡

የኢዜአ ሪፖርተር በከተማው ተዘዋውሮ እንደተመለከተው ዛሬ በከተማ የተካሄደው ሰልፍ ካለፉት ሁለት ቀናት የበለጠ  አብዛኛውን የከተማው  አካባቢ ያዳረሰ ነው ፡፡

በነበረው ግርግር በሰውና ንብረት ላይ ጉዳት መድረሱንና አገልግሎት መሰጪዎች መሰተጓጎላቸውን ተመልክቷል፡፡

በጤና ጣቢያዎችና በድል ጮራ ሆስፒታል የኢዜአ ሪፖርተር ባደረገው ቅኝት  የተጎዱ ሰዎች ህክምና አግኝተው ሲመለሱ አይቷል፡፡

ሪፖርተራችን በጉዳዩ ዙሪያ ምላሽ ለማግኘት በተደጋጋሚ ወደ ፖሊስ ኮሚሽን ህዝብ ግንኙነት ፣ የመንግስት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮና የአስተዳደሩ አመራሮች ጋር ያደረገው የአካልና  የስልክ ሙከራ አልተሳካም፡፡

የመከላከያ ሠራዊት አባላት የወጣቶቹ ቁጣ  በሰላማዊ መንገድ  ለማብረድና ለማረጋጋት ያደረጉት ጥረት  በሰልፍ አድራጊዎችና በሌላም ህብረተሰብ ዘንድ በአዎንታዊ ጎኑ ድጋፍ አግኝቷል፡፡

በአሁን ሰዓት ሰራዊቱ በድንጋይ የተዘጉትን መንገዶች በማጽዳት ለተሸከርከሪዎች ክፍት እንዲሆኑ በቅንጅት እየሰራ መሆኑን ለማወቅ ተችሏል፡፡

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም