ኬር ኢትዮጵያ በ7 ነጥብ 6 ሚሊየን ብር ወጭ ያስገነባውን የምርምርና የስልጠና ማዕከል ለሐረማያ ዩኒቨርሲቲ አስረከበ

82

ሐረር ጥር 5/2011 ኬር ኢትዮጵያ በምስራቅ ሐረርጌ ዞን ኩርፋ ጨሌ ወረዳ በ7 ነጥብ 6 ሚሊየን ብር ወጭ ያስገነባውንና የእንስሳት ምርምርና የአርሶ አደሮች ማስልጠኛ ማዕከል ለሐረማያ ዩኒቨርሲቲ አስረከበ፡፡

በኬር ኢትዮጵያ የምሥራቅ ሐረርጌ ፕሮግራም ሥራ አስኪያጅ አቶ ሆሳዕና ኃይለማርያም  በርክክቡ ሥነ ሥርዓት ላይ እንደተናገሩት ማዕከሉ ለእንስሳት እርባታ፣ ድለባና የዝናብ እጥረት ተቋቁመው ምርት የሚሰጡ የአዝዕርት ሰብሎች ላይ ምርምር ያካሂድበታል፡፡

ማዕከሉ ዩኒቨርሲቲው በተለያዩ አካባቢዎች የሚያከናውናቸውን የምርምር ሥራዎች እንደሚያጠናከርለትም አመልክተዋል፡፡

የዩኒቨርሲቲው የምርምር ጣቢያዎች ዳይሬክተር አቶ አድምቀው ኃይሉ በበኩላቸው ማዕከሉ በምሥራቅ ኢትዮጵያ የእንስሳት ሀብት ልማትን ለማጎጎልበት ከአርሶና አርብቶ አደሮች ለሚያደርገው እንቅስቃሴ ጥረት ተጨማሪ አቅም ይፈጥርለታል ብለዋል፡፡

በዚህም የሚገኙ የገበሬዎች ማሰልጠኛ ተቋማትን በመጠቀም ለአርብቶና አርሶ አደሮች በእንስሳት አመጋገብ፣አያያዝ፣ርባታና ድለባ ስልጠና በመስጠት ላይ እንደሚገኝ አመልክተዋል፡፡

የእንስሳት ጤና ተማሪዎችንና ባለሙያዎችን በመጠቀም የህክምና አገልግሎት እንደሚሰጥ አስረድተዋል።

የኩርፋጨሌ ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ አልዪ ጠለሀ  ዩኒቨርሲቲው የአካባቢውን ማህበረሰብና አርሶ አደሩን በምርጥ ዘር ስርጭትና በሌሎች የማህበረሰብ አገልግሎት ተጠቃሚ እያደረገ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

ማዕከሉ ኩርፋ ጨሌን ጨምሮ የሦስት ወረዳዎች አርሶና አርብቶ አደሮች በምርምር የሚያገኟቸውን የእንስሳትም ሆነ የሰብል ዝርያዎችን  እንዲጠቀምና የቴክኖሎጂ ተጋሪ እንዲሆን ያደርጉታል ብለዋል፡፡

የኩርፋ ጨሌ ወረዳ ሁላጀነታ ቀበሌ ነዋሪዋ  ከፊል አርሶ አደር መፍቱሃ አብዱላሂ ዩኒቨርሲቲው ምርጥ የድንችና የሰብል ዝርያዎችን በማሰራጨት ምርታቸውን እንዳሳደገላቸው ተናግረዋል፡፡

"በአሁኑ ወቅት የድለባ  ከብት ተሰጥቶኝ የማድለብ ሥራ ጀምሬያለሁ" ያሉት አስተያየት ሰጪዋ፣በቀጣይም ዩኒቨርሲቲው የሰብል በሽታን ለመከላከል ድጋፍ እንዲያደርግላቸው ጠይቀዋል፡፡

የዚሁ ቀበሌ ሌላዋ ነዋሪ  ወይዘሮ ፋጡማ አህመድ በበኩላቸው ዩኒቨርሲቲው ማዕከሉን መረከቡ ሥራቸውን በተሻለ ሁኔታ ለማከናውንና ስልጠና ለማግኘት ያስችለኛል ብለው እንደሚያምኑ አስታውቀዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም