በአጋሮ ከተማ አምስት የመድኃኒት መሸጫ መደብሮች ታገዱ - ኢዜአ አማርኛ
በአጋሮ ከተማ አምስት የመድኃኒት መሸጫ መደብሮች ታገዱ
77
ጅማ ጥር4/52011 የአጋሮ ከተማ ጤና ጥበቃ ጽህፈት ቤት በህገ-ወጥ ተግባር ላይ ተሰማርተዋል ያላቸውን አምስት መድኃኒት መሸጫ መደብሮች ማገዱን አስታወቀ።
የጽህፈት ቤቱ ኃላፊ አቶ ሃፊዝ ጀማል ለኢዜአ ንደገለጹት የመድኃኒት መደብሮቹ ላይ እገዳው የተጣለው በገበያ ውስጥ የሚዘዋወሩ ህገ-ወጥ መድኃኒቶችን ለማስቆም እየተደረገ ባለው ቁጥጥር ነው።
"የመድኃኒት መደብሮቹ ያልተፈቀደ መድኃኒት ይዘው በመገኘታቸው፣ ጊዜ ያለፈባቸው መድኃኒቶች ለገበያ በማቅረባቸው፣ ከመድኃኒት ጋር የመዋቢያ ምርቶችን ሲሸጡና የመድኃኒት አያያዛቸው ደካማ መሆኑ ስለተደረሰበት እገዳ ተጥሎባቸዋል" ብለዋል ።
በመደብሮቹ ላይ እንደየ ጥፋታቸው ከ 20 ቀን እስከ አምስት ወር የሚደርስ የአገልግሎት እገዳ የተጣለባቸው መሆኑን ተናግረዋል ።
ፈዋሽ ያልሆኑ ህገ-ወጥ መድኃኒቶች በገበያ ላይ እንደሚገኙ የጠቆሙት ኃላፊው ህብረሰተሰቡ መድኃኒቶችን ሲገዛም ሆነ ሲጠቀም የህክምና ባለሙያዎች እያማከረ ጥንቃቄ ማድረግ እንዳለበትም አሳስበዋል፡፡
ህብረተሰቡ ህገ-ወጥ መድኃኒቶች ሲያጋጥሙት ለመድኃኒት ተቆጣጣሪዎችና ለጸጥታ አካላት መረጃ በመስጠት እንዲተባበር መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡