ያለ ሰላም ልማትና ዴሞክራሲን ማሰብ አይቻልም---የኢፌዴሪ የሰላም ሚኒስቴር

92
ሀዋሳ ታህሳስ 2/2011 ሰላም በሌለበት ልማት፣ዴሞክራሲና የተረጋጋ ሕይወትን ማሰብ እንደማይቻል የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ የሰላም ሚኒስቴር አስታወቀ። ከዘጠኙ ክልሎችና ከሁለት የከተማ አስተዳደሮች የተወጣጡ የሰላም አምባሳደር እናቶች ዛሬ ከሃዋሳ ከተማ ነዋሪዎች ጋር ተወያይተዋል። በውይይቱ ላይም የሰላም ሚኒስቴር ተወካይ የሆኑት ወይዘሮ አበባ ተገኝ እንዳሉት በሃገሪቱ አንዳንድ አካባቢዎች የተከሰተው የጸጥታ ችግር እንዲቆም መላው ህብረተሰብ በትኩረት ሊሰራ ይገባል። "ያለ ሰላም ልማት ዴሞክራሲና እድገት አይኖርም" ያሉት ተወካይዋ ሴቶች በሰላም እጦት ምክንያት ዋነኛ ተጎጂዎች በመሆናቸው ለዘላቂ ሰላም መረጋገጥ ሁሉም ህብረተሰብ ከሴቶች ጎን እንዲቆም ጠይቀዋል። ወጣቱ የሃገር ተረካቢ እንዲሆን ወላጆች ማስተማር ብቻ ሳይሆን በመልካም ስነ-ምግባር በማነጽና በመቆጣጠር ለጸረ-ሰላም ኃይሎች መጠቀሚያ እንዳይሆን ማድረግ እንዳለባቸውም ገልጸዋል። የሰላም አምባሳደርና የልኡካን ቡድኑ አባል የሃረሪ ክልል ተወካይ ወይዘሮ ገነት አሰፋ በበኩላቸው ሁሉም በየአካባቢው ያሉ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎችን እንደ ልጆቹ በመጠበቅ በሰላም እጦት እንዳይጎዱ ሊከላከል እንደሚገባ አስረድተዋል። የሰላም አምባሳደሮቹ በዛሬው እለት የተወያዩባቸውን የሃላባና ሃዋሳ ከተሞች ነዋሪዎችን ጨምሮ በሃገሪቱ የተለያዩ ከተሞች በመዘዋወር ተመሳሳይ ውይይት አድርገዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም