የነዳጅ አቅርቦትና ፍላጎት ባለመጣጣሙ በየጊዜው የነዳጅ እጥረቱ እየጨመረ መጥቷል

134
አዲስ አበባ ታህሳስ 1/2011 በነዳጅ አቅርቦትና ፍላጎት አለመጣጣም ምክንያት በየጊዜው የነዳጅ እጥረቱ እየጨመረ መምጣቱን የነዳጅ አቅራቢ ኩባንያዎች ገለጹ። ነዳጅ በህገወጥ መንገድ ከአገር እንዲወጣ እየተደረገ መሆኑም የእጥረቱ መንስኤ መሆኑም ተጠቁሟል። መንግስት በአሁኑ ወቅት በቂ የሆነ ነዳጅ ወደ አገር ውስጥ በማስገባትና ለኩባንያዎቹ በፍትሃዊነት እንዲዳረስ እያደረገ መሆኑን የማዕድን፣ ነዳጅና የተፈጥሮ ጋዝ ሚኒስቴር ገልጿል። ሚኒስቴሩ ዛሬ የነዳጅ ስርጭት፣ ጥራትና ብክነት ዙሪያ ከነዳጅ አቅራቢ ኩባንያዎችና ባለድርሻ አካላት ጋር ተወያይቷል። ኩባንያዎቹ እንዳመለከቱት፤ በአሁኑ ወቅት በአዲስ አበባ ከተማ ሲታይ የነበረው የነዳጅ አቅርቦት ችግር የተረጋጋ ቢሆንም በክልል ከተሞች እጥረቱ አለ። ለእጥረቱ መንስዔም በአገሪቱ ያሉት የነዳጅ ማደያዎች ቁጥር አነስተኛ በመሆኑ የአቅርቦትና ፍላጎት ባለመጣጣም  ችግሩ እንዲባባስ አድርጎታል። በተለይ በክልል ከተሞች ችግሩ እንዲባባስ ያደረገው ለትራንስፖርት፣ ለእርሻ ተሽከርካሪዎች፣ ለመብራትና ለሌሎች አገልግሎቶች የነዳጅ ፍላጎቱ በየጊዜው እየጨመረ በመምጣቱ እንደሆነ አቅራቢ ኩባንያዎቹ አብራርተዋል። የኢትዮጵያ ነዳጅ ድርጅት ዋና ዳይሬክተር አቶ ታደሰ ኃይለማርያም እንዳሉት በአገሪቱ እየተፈጠረ ያለው የነዳጅ አቅርቦትና ስርጭት እጥረት ብቻ ሳይሆን በህገ ወጥ መንገድ ከአገር እንደሚወጣ የሚያመላክቱ ማስረጃዎች አሉ። በአሁኑ ወቅት ሶማሌ ላንድን ጨምሮ ወደ ሌሎች የጎረቤት አገሮች የቤንዚንና ናፍታ ምርቶች በኮንትሮባንድ ከአገር እየወጣ እንደሚገኝ ጠቁመዋል። ማዕድን ነዳጅና የተፈጥሮ ጋዝ ሚኒስትር ዶክተር ሳሙኤል ሁርጶ በበኩላቸው መንግስት በአሁኑ ወቅት በቂ የሆነ ነዳጅ ወደ አገር ውስጥ በማስገባትና ለኩባንያዎች እንዲዳረስ እያደረገ መሆኑን ተናግረዋል። በኩባንያዎቹ በኩል የሚነሱ የአቅርቦትና ፍላጎት አለመጣጣም ችግሮች እንደ መልካም አጋጣሚ በመመልከት መሠረተ ልማቱን በማስፋፋት ችግሮቹ እንዲቃለሉ ማድረግ ያስፈልጋል ብለዋል። በተለይ የነዳጅ ማደያዎች ቁጥር የሚጨመርበትን፣ ፍላጎትና አቅርቦትን ችግር ተለይቶ አስፈላጊው ማስተካከያ የሚደረግበት ሥራ እንደሚሰራም ጠቁመዋል። በዘርፉ እየታየ ያለውን የአቅርቦትም ሆነ የስርጭት ፍትሃዊነትን ለመፍታትና ህገ ወጥ ንግድን ለመከላከል ከኢትዮጵያ ነዳጅ ድርጅት እና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ጋር ሚኒስቴሩ በትብብር እንደሚሰራ አመልክተዋል።  
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም