በመቀሌ የህግ-የበላይነት እንዲረጋገጥ የሚጠይቅ ህዝባዊ ሰልፍ ሊካሔድ ነው

65
መቀሌ ህዳር 25/2011 በመቀሌ ከተማ የፊታችን ቅዳሜ የሚከበረው የብሄሮች፣ ብሄረሰቦችና ህዝቦች ቀን በዓል የህግ የበላይነትና ህገ-መንግስቱ ይከበር የሚል መልዕክት የሚተላለፍበት መሆኑን የከተማው የመንግስት ኮሙኒኬሽን ፅህፈት ቤት አስታወቀ። ፅህፈት ቤቱ በበአሉ አከባበር ዙሪያ ዛሬ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥቷል። የፅህፈት ቤቱ ኃላፊ አቶ ዘመንፈስቅዱስ ፍስሃ በመግለጫቸው እንዳስታወቁት የዘንድሮ የብሔሮች ፣ ብሄረሰቦችና ህዝቦች ቀን በዓል በክልል ደረጃ የፊታችን ቅዳሜ በመቀሌ ከተማ በህዝባዊ ሰልፍ ይከበራል። "በህዝባዊ ሰልፉ በአንዳንድ የሀገሪቱ አካባቢዎች እየተከሰቱ ያሉ ዘርን መሰረት ያደረጉ ጥቃቶች ይቁሙ፤ የህግ የባላይነትና ህገ-መንግስቱ ይከበር የሚሉ መልዕክቶች የሚተላለፉበት ነው" ብለዋል። "የትግራይን ህዝብ ለማምበርከክ የሚደረጉ ሴራዎች ተቀባይነት እንደሌላቸው በሰልፉ መልዕክት ይተላለፋል" ሲሉም ተናግረዋል፡፡ "በማንነት ጥያቄና በአዋሳኝ አካባቢዎች ምክንያት በማድረግ የክልሉን ህዝብ የሚነኩ ትንኮሳዎች ተቀባይነት የላቸውም" ያሉት ኃላፊው በውጭ ጣልቃ-ገብነትና የውስጥ ሴራዎች እንዲቆሙ የሚያስገነዝቡ መልዕክቶች በሰልፉ እንደሚተላለፉ አመላክተዋል። "ህዳር 29 ህገ-መንግስቱ የፀደቀበት በመሆኑ የህገ-መንግስቱ ልዕልናን የሚያጎሉ መልዕክቶች በሰልፉ ጎልተው ይወጣሉ" ብለዋል። በዓሉን በህዝባዊ ሰልፉ በ"ባሎኒ" ስታድዮም በድምቀት ለማክበር ዝግጅት መደረጉን የገለፁት ኃላፊው በሰልፍ ላይ ከ200 ሺህ በላይ የከተማውና አካባቢው ህዝብ ይሳተፋል ተብሎ እንደሚጠበቅ አመላክተዋል።  
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም