ኮሚሽኑ የተፈናቀሉ ዜጎችን ወደ ቀያቸው ለመመለስ የቅድመ ዝግጅት ስራ እየሰራ ነው

94
አዲስ አበባ መስከረም 26/2011 ከቤኒሻንጉል ጉምዝ ክልል የተፈናቀሉ ዜጎችን ወደ ቀያቸው ለመመለስ ከአካባቢው ነዋሪዎችና ከአገር ሽማግሌዎች ጋር ለመስራት በዝግጅት ላይ መሆኑን የብሔራዊ አደጋ ስጋትና ስራ አመራር ኮሚሽን አስታወቀ። የአካባቢው ነዋሪዎችና ለጋሽ ድርጅቶች የተፈናቀሉ ዜጎችን ለመርዳት ያሳዩት ተነሳሽነት ከፍተኛ ቢሆንም ከችግሩ ስፋት አንጻር ተጨማሪ ድጋፍ እንደሚያስፈልግ ተገልጿል። የኮሚሽኑ የህዝብ ግንኙነትና ኮሙኒኬሽን ዳይሬክተር አቶ ደበበ ዘውዴ ለኢዜአ እንደተናገሩት የተፈናቀሉ ዜጎችን ወደ ቀያቸው ለመመለስ በባህላዊና ሃይማኖታዊ ስነ-ስርዓት ዕርቅ ለማውረድ የቅድመ ዝግጅት ስራዎች እየተሰሩ ነው። በተለይ የሃይማኖት አባቶች፣ የአገር ሽማግሌዎች፣ ወጣቶች፣ የየአካባቢው ነዋሪዎችና የመንግስት አካላት በተገኙበት እርቅና ሰላም የማውረድ ስራ ይሰራል ብለዋል። ኮሚሽኑ ተፈናቃዮቹ ከሚገኙበት የኦሮሚያ ክልል መንግስት ጋር በቅንጅት በመስራት ላይ ሲሆን ድጋፉን ለማጠናከር ተጨማሪ የባለሙያዎች ቡድን ወደ ስፍራው መላኩንም ገልጸዋል። ኮሚሽኑ እስካሁን ከአካባቢው ለተፈናቀሉ ዜጎች 17 ሺህ 468 ኩንታል ስንዴ ሩዝና አልሚ ምግብ፣ 146 ሺህ 194 የመመገቢያ ቁሳቁስ መጠለያና አልባሳትና 1 ሺህ 101 ካርቶን የዱቄት ወተት ወደ ስፍራው መላኩን ገልጸዋል። ከዚህ በተጨማሪ ለተፈናቀሉ ዜጎች ከዳሸን ባንክ አምስት ሚሊዮን ብር ድጋፍ ሲደረግ ከቡራዩና አካባቢዋ ለተፈናቀሉም እንዲሁ በሲውዘርላንድ የሚገኙ ትውልደ ኢትዮጵያዊያንና ኤርትራዊያን 600 ሺህ ብር ድጋፍ አድርገዋል። ኮሚሽኑ እንዳስታወቀው ሰሞኑን ከቤኒሻንጉል ጉምዝ ክልል ተፈናቅለው በምዕራብና ምስራቅ ወለጋ 10 ወረዳዎች የሚገኙ ሰዎች ቁጥር 91 ሺህ 348 ደርሷል። በተጨማሪ በመላው አገሪቱ በመደበኛነት በድርቅ አደጋ የሚረዱ ከሰባት ሚሊዮን በላይ ዜጎች ያሉ ሲሆን ለጋሽ አካላት የተለመደ ትብብራቸው እንዲያደርጉ ጠይቋል። በተለይ ዲያስፖራው፣ ባለሃብቶችና ሌሎችም ድጋፍ እንዲያደርጉ ጥሪ የቀረበ ሲሆን ይህንን ለመምራት የሚያስችል ኮሚቴ መዋቀሩንም ገልጸዋል። በቅርቡ በምዕራብ ጉጂ፣ በጌዲኦ፣ በሶማሌና በቡራዩ የተፈናቀሉ ዜጎችን ወደ ቀያቸው ለመመለስ በባህላዊ ስነ-ስርዓት የሕዝብ ለሕዝብ ስራ መሰራቱ ይታወሳል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም