በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሚከሰቱ የጸጥታ ችግሮችን አስቀድሞ ለመከላከል እንዲቻል ህዝባዊ ወይይት ይካሄዳል

111
አዲስ አበባ መስከረም 25/2011 በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሚከሰቱ የጸጥታ ችግሮችን አስቀድሞ መከላከል እንዲቻል በአገር አቀፍ ደረጃ ህዝባዊ ውይይት እንደሚካሄድ የትምህርት ሚንስትር ዶክተር ጥላዬ ጌቴ ተናገሩ። ጠቅላይ ሚንስትር ዶክተር አብይ አህመድ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማትን ሰላማዊና ደህንነታቸው የተረጋገጠ ለማድረግ ከዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንቶችና ከክልል ርዕሰ መስተዳድሮች ጋር መወያየታቸውንም አክለዋል። ባለፈው የትምህርት ዘመን በተወሰኑ የመንግስት የከፍተኛ ተቋማት በተነሱ ግርግሮች ምክንያት የሰው ህይወት ማለፉና ንብረት መውደሙ ይታወሳል። የትምህርት ሚንስትሩ ዶክተር ጥላዬ ጌቴ በተለይ ለኢዜአ እንደተናገሩት፤ በዘንድሮው የትምህርት ዘመን መሰል ችግሮች እንዳይከሰቱ ጥቅምት 2 ቀን 2011 ዓ.ም  ሁሉንም ባለድርሻ አካላት የሚሳተፉበት ህዝባዊ ውይይት በተለያዩ የአገሪቷ አካባቢዎች ይካሄዳል። "በትምህርት ተቋማት ውስጥ የተማሪዎች ዋነኛ ተግባር መማርና መመራመር ነው" ያሉት ሚንስትሩ፤ መንግስት ተቋማቱ ከማንኛውም የጸጥታ ችግር ነጻ ሆነው አገልግሎት እንዲሰጡ ከመቸውም ጊዜ በላይ አበክሮ እንደሚሰራ ተናግረዋል። ጠቅላይ ሚንስትር ዶክተር አብይ አህመድ ከ11ኛው የኢህአዴግ ጉባኤ ጎን ለጎን የጸጥታ አካላትን ባሳተፈ መልኩ ከዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንቶች እና ከክልል ርዕሰ መስተዳድሮች ስለ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የጸጥታ ችግሮችና መፍትሄዎቻቸው መወያየታቸውንም አውስተዋል። ይህም መንግስት ለጉዳዩ ትኩረት መስጠቱን እንደሚያሳይ ገልጸው፤ ዘንድሮ ወደ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሚቀላቀሉ ተማሪዎች ወደ መደበኛ የመማር ማስተማር ሂደት ከመመለሳቸው በፊት ውይይት እንደሚያደርጉም ተናግረዋል። በተያያዘ ዜና ዶክተር ጥላዬ ጌቴ በትምህርት ፍኖተ ካርታ ላይ ከባለድርሻ አካላት ጋር የተካሄደው ውይይት በርካታ ጠቃሚ ግብአቶች የተገኙበት እንደነበረ ጠቁመዋል። በቅርቡ ፍኖተ ካርታውን በተመለከተ "የተለያዩ ህብረተሰብ ክፍሎች የሚሳተፉበት ትልቅ ህዝባዊ ውይይት በአዳማ ከተማ ይዘጋጃል" ብለዋል። እስካሁን ባለው ሂደት የተገኙ ግብዓቶችን በማካተት ፍኖተ ካርታው እንደሚሻሻልም ገልጸዋል። በዘንድሮው የትምህርት ዘመን  የከፍተኛ ትምህርት ተቋማትን መግቢያ ያሟሉ 149 ሺህ ተማሪዎች በተለያዩ የመንግስት ዩኒቨርሲቲዎች    መመደባቸውን ከትምህርት ሚንስቴር የተገኘ መረጃ ያመለክታል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም