የኢትዮጵያ ኢንደስትሪ ፖርኮች ልማት ኮርፖሬሽን የሠመራ ኢንደስትሪ ፓርክን ወደስራ ለማስገባት እየሰራ ነው

184

ሠመራ ፤ ታህሳስ 18 ቀን 2015(ኢዜአ) ፡- ለወደብ በቅርበት የሚገኘውን የሠመራ ኢንደስትሪ ፖርክን ወደስራ ለማስገባት በትኩረት እየተሰራ መሆኑን የኢትዮጵያ ኢንደስትሪ ፖርኮች ልማት ኮርፖሬሽን አስታወቀ።

የኮርፖሬሽኑ ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎች ዛሬ ፖርኩን ተዘዋውረው ጎብኝተዋል።

በጉብኝቱ ወቅት  የኮርፖሬሽኑ  ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ አክሊሉ ታደሰ ፤ባለፉት ሁለት ዓመታት በሀገሪቱ ተከሰቶ የነበረው  የጸጥታ ችግር  በመፈታቱ ኢንደስትሪ ፖርኮች ኢንቨስትመንትን ለመሳብ እየተሰሩ እንደሚገኝ አስታውቀዋል።

ኮርፖሬሽኑ በበጀት ዓመቱ ትኩረት ከሰጣቸው  መካከል የሠመራ ኢንደስትሪ ፖርክን ወደስራ ማስገባት አንዱና ዋነኛው መሆኑን ገልጸዋል።

የጉብኝቱ ዓላማም  ፖርኩ ያለበትን ተጨባጭ ሁኔታ ገምግሞ  ክፍተቶቹን በአጭር ጊዜ ውስጥ ተስተካክለው በተሟላ ሁኔታ ወደ ስራ እንዲገባ ምቹ ሁኔታ ለመፍጠር መሆኑን አስረድተዋል።

ፓርኩ ውስጥ ለሚሰማሩ ባለሃብቶት የተሟላ አገልግሎት መስጠት የሚያስችሉ የኤሌክትሪክና ውሃ አቅርቦት እንዲሁም የፍሳሽ ማስወገጃን ጨምሮ ተያያዥ የማጠናቀቂያ  ስራዎች በፍጥነት ለማከናወን ከግንባታ ተቋራጩ ጋር  መግባባት ላይ መደረሱን ተናግረዋል።



በተጨማሪም ፖርኩ ለወደብ ያለውን ቅርበትና በአካባቢው ያለውን እምቅ ሃብት ማልማት ለሚችሉ የሀገር ውስጥና የውጭ ባለሃብቶች ወደ ፖርኩ ገብተው ማምረት እንዲጀምሩ የሚያስችል  የማስተዋወቅ ስራዎችን ኮርፖሬሽኑ በትኩረት እየሰራ  ይገኛል ብለዋል

የሠመራ ኢንደስትሪ ፓርክ   ስራ አስኪያጅ አቶ አህመድ ሃሰን በበኩላቸው፤ ፖርኩ በ50 ሄክታር መሬት ላይ ያረፈና ስምንት  የማምረቻ ሼዶች እንዳሉት ገልጸዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም