የጋምቤላ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን የተለያዩ ህገ ወጥ የጦር መሳሪያዎችን በቁጥጥር ሥር አዋለ

194
ጋምቤላ መስከረም በ13/2011 የጋምቤላ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን የተለያዩ ህገ ወጥ የጦር መሳሪያዎችን ከአንድ ተጠርጣሪ ግለሰብ ጋር በቁጥጥር ሥር ማዋሉን አስታወቀ። የክልሉ ፖሊስ ኮሚሽን ከሚሽነር ቾል ኩን ዛሬ ለኢዜአ እንደገለጹት ህገ ወጥ መሳሪያዎችን ትናንት በጋምቤላ ከተማ በቁጥጥር ሥር ማዋል የተቻለው ከላሬ ወረዳ ወደ ጋምቤላ ከተማ ለማስገባት ሲሞክር ነው። በፖሊስ ከተያዙት የጦር መሳሪያዎች መካከል አራት ሽጉጦች፣ አንድ ታጣፊ ክላሽ፣ አንድ ሺህ 133 የተለያዩ ዓይነት ጥይቶች ይገኙበታል። ከህገ ወጥ የጦር መሳሪያዎች ጋር ከ20 ሺህ 600 ብር በላይ ገንዘብ ፖሊስ አብሮ በቁጥጥር ሥር መዋሉንም ኮሚሽነሩ ተናግረዋል። በተጠርጣሪው ላይ በተደረገው ማጣራትም የጦር መሳሪያዎቹን ወደ መሀል ሀገር የማስገባት እቅድ እንደነበረውም ኮሚሽነሩ ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅት በተጠርጣሪ ግለሰቡ ላይ ማስረጃ የማሰባሰብና የማጠራት ሥራ እየተካሄደ እንደሚገኝ ጠቁመው፣ "የምርመራ ሂደቱ እንደተጠናቀቀ ጉዳዩ ወደ ፍርድ ቤት ይላካል" ብለዋል። ክልሉ በተለይም ከደቡብ ሱዳን ጋር በስፋት በድንበር የሚዋሰን ከመሆኑ ጋር ተያይዞ በርካታ ህገ ወጥ የጦር መሳሪያ ወደ ክልሉ እየገባ መሆኑን የገለጹት ኮሚሽነሩ፣ ህገ ወጥ የጦር መሳሪያ ዝውውርን ለመግታት በሚደረገው ጥረት የህዝቡ ተሳተፎውን እንዲያጠናክር ጠይቀዋል። ህግ ወጥ የጦር መሳሪዎች በሀገሪቱ ላይ ሊያስከትሉ የሚችሉትን ማህበራዊና ኢኮኖሚዊ ችግሮች በመገንዘብ ኮሚሽነሩ የህዝብ ንቅናቄ በመፍጠር በጋራ ለመከላከል ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በክልሉ በተመሳሳይ መልኩ 69 ህገ ወጥ የጦር መሳሪያዎች ከአንድ ወር በፊት በፖሊስ በቁጥጥር ስር መዋላቸው ይታወሳል ።          
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም