በአዲስ አበባ ከ7 ነጥብ 6 ቢሊዮን ብር በላይ ወጪ ሁለት ሜጋ ፕሮጀክቶችን ግንባታ ለማስጀመር የፊርማ ስነ-ስርዓት ተካሄደ

142

መስከረም 26 ቀን 2015 (ኢዜአ) በአዲስ አበባ ከተማ ከ7 ነጥብ 6 ቢሊዮን ብር በላይ ወጪ የሁለት ሜጋ ፕሮጀክቶችን ግንባታ ለማካሄድ የፊርማ ስነ-ስርዓት መከናወኑ ተገለጸ።

ፕሮጀክቶቹ የግብርና ምርቶች መሸጫ ማዕከላት እና የዘውዲቱ ሆስፒታል የማስፋፍያ ግንባታ መሆናቸውን የአዲስ አበባ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገልጸዋል።

ከንቲባ አዳነች “ዛሬ ለከተማችን አዲስ አበባ ተጨማሪ ብስራት የሆኑ ከ7 ነጥብ 6 ቢሊዮን ብር በላይ ወጪ ሁለት ሜጋ ፕሮጀክቶችን ግንባታ ለማስጀመር የፊርማ ስነ-ስርዓት አከናውነናል” ብለዋል፡፡

የመጀመሪያው ፕሮጀክት ከ6 ነጥብ 1 ቢሊዮን ብር በላይ ወጪ በለሚ ኩራ እና በኮልፌ ክፍለ ከተሞች የሚገነቡ ሶስት የግብርና ምርቶች መሸጫ ማዕከላት መሆኑን ጠቅሰው ሁለተኛው ደግሞ በ1 ነጥብ 5 ቢሊየን ብር የሚገነባ ባለ 8 ወለል የዘውዲቱ ሆስፒታል ማስፋፍያ ፕሮጀክት መሆኑን ገልጸዋል።

የግብርና ምርቶች መሸጫ ማዕከላቱ በከተማው አስተማማኝ የግብርና ምርቶች አቅርቦት እንዲኖር የሚያግዝና ገበያን በማረጋጋት ለሸማቹ በተመጣጣኝ ዋጋ እንዲቀርብ የሚያደርግ ነው ፡፡

የሆስፒታሉ ማስፋፊያ ደግሞ የጤናውን ዘርፍ ለማሳደግ በተያዘው ቁርጠኝነት የሚገነባ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡

ግንባታው 200 የህሙማን አልጋዎች፣27 የድንገተኛ ክፍል ህክምና መስጫ ክፍሎች፣ የቀዶ ጥገናና የፊዝዮቴራፒ ህክምናዎችን ጨምሮ አዳራሾችን ያካተተ መሆኑን ከንቲባዋ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ገልጸዋል፡፡

የግብርና ምርቶች መሸጫ ማዕከላት ግንባታ በአዳዲስ ቴክኖሎጂዎች በፍጥነት ጀምሮ በማጠናቀቅ ተሞክሮ ያለው ኦቪድ ግሩፕ በተሰኘ ድርጅት እንደሚገነባም አመላክተዋል።

የሆስፒታል ማስፋፊያ ግንባታ በዘርፉ ልምድ ባካበተ ኮንስትራክሽን ኩባንያ የሚገነባ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡

ፕሮጀክቶቹ በተቀመጠላቸው ጊዜና ጥራት በማጠናቀቅ ህብረተሰቡን ተጠቃሚ እንዲሆን ይደረጋል ነው ያሉት።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም