ቤተክርስቲያኗ ምዕመኑ የመስቀል ደመራ በዓልን መንፈሳዊ ይዘቱን በጠበቀ መንገድ እና በክርስቲያናዊ ሥነ ምግባር እንዲያከብር ጥሪ አቀረበች

110

መስከረም 13 ቀን 2015 (ኢዜአ)የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ህዝበ ክርስቲያኑ የመስቀል ደመራ በዓልን መንፈሳዊ ይዘቱን በጠበቀ መንገድ እና በክርስቲያናዊ ሥነ ምግባር እንዲያከብር መልዕክት አስተላለች።

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅና የባህር ዳር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ አብርሃም የ2015 ዓ.ም የመስቀል ደመራ በዓልን አስመልክቶ ለመገናኛ ብዙሃን መግለጫ ሰጥተዋል።

በመግለጫቸው የመስቀል ደመራ በዓል ያለምንም የጸጥታ ችግር በሰላም እንዲከበር ቅድመ ዝግጅት መደረጉን ተናግረዋል።

ለዚህም በቤተክርስቲያኗ በኩል የተለያዩ ኮሚቴዎች ተቋቁመው ከመንግስት የጸጥታ አካላት ጋር በቅንጅት እየተሰራ እንደሆነም አስረድተዋል።

ህዝበ ክርስቲያኑ የመስቀል ደመራ በዓልን መንፈሳዊ ይዘቱን በጠበቀ መንገድ እና ክርስቲያናዊ ሥነ ምግባርን በተላበሰ ሁኔታ እንዲከበር መልዕክት አስተላልዋል።

ምዕመኑ የመስቀል ደመራ በዓልን ለማክበር ወደ መስቀል አደባባይ ሲመጣ የቤተክርስቲያኗን ስርዓት የሚገልፅ አለባበስ ለብሶ መምጣት እንዳለበት አሳስበዋል።

በበዓሉ ላይ ፖለቲካዊ ይዘት ያላቸው፣ ሃይማኖትን ከሃይማኖት የሚያጋጩ መልዕክቶችንና ዓርማዎችን ይዞ መግባት የተከለከለ መሆኑንም አስታውቀዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ አብርሃም አክለውም ለመላው የክርስትና እምነት ተከታዮች በዓሉ የፍቅር የሰላምና የአንድት እንዲሆን እንዲሆን ተመኝተዋል፡፡

ህዝበ ክርስቲያኑ በዓሉን የተቸገሩትን በመርዳት፣የታመሙትን በመጠየቅ እንዲያከብርም መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም