ዶክተር ቴድሮስ የአሸባሪው ሕወሃት ቡድንን እኩይ ተግባር በመደገፍ ኢትዮጵያ ላይ ሃሰተኛ መረጃ እያሰራጩ ነው-በተመድ የኢትዮጵያ ቋሚ መልእክተኛ ጽህፈት ቤት

652

ነሐሴ 27 ቀን 2014 (ኢዜአ) የአለም የጤና ድርጅት ዳይሬክተር ዶክተር ቴድሮስ አድሃኖም የአሸባሪ ሕወሃት ቡድንን እኩይ ተግባር በመደገፍ ኢትዮጵያ ላይ ሃሰተኛ መረጃ እያሰራጩ ነው ሲል በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የኢትዮጵያ ቋሚ መልእክተኛ ጽህፈት ቤት ገለጸ።

ጽህፈት ቤቱ ዶክተር ቴድሮስ ኢትዮጵያን በተመለከተ እያሰራጩ የሚገኙትን የሐሰት ፕሮፖጋንዳ አውግዟል።

የዓለም ጤና ድርጅት ዶክተር ቴድሮስ ከድርጅቱ ስነ ምግባር ያፈነገጠ ድርጊትን በፍጥነት እንዲያስቆምም የኢትዮጵያ ቋሚ መልእክተኛ ጽህፈት ቤት ጠይቋል።

የቡድኑ ቆንጮ አመራር የነበሩት ዶክተር ቴድሮስ አሁንም ከዋና ትእዛዝ ሰጪ አመራሮች መካከል አንዱ በመሆን ቡድኑን በማገልገል ላይ የሚገኙ ሲሆን በኢትዮጵያ መንግስት ላይ ያነጣጠረ የሐሰት ፕሮፖጋንዳ እያሰራጩ ይገኛሉ ብሏል ጽህፈት ቤቱ።

ዶክተር ቴድሮስ የአሸባሪውን እኩይ ተግባራት ይደግፋሉ ያለው ጽህፈት ቤቱ ፤ቡድኑ በአፋር እና አማራ ክልሎች ከፍተኛ ውድመት ሲያደርስ ተግባሩን አጋልጠው አያውቁም ብሏል።

ሌሎች አለም አቀፍ ተቋማት በቡድኑ ምክንያት የፈረሱትን የጤና ተቋማት ለመስራት ሲረባረቡ ዶክተር ቴድሮስ አድሃኖም ዝምታ መምረጣቸውን ነው የገለጸው ።

የሽብር ቡድኑ በአጎራባች ክልሎች ጦርነት በመክፈት በርካቶችን ሲጨፈጭፍ ፤ትምህርት ቤቶችን ፤የጤና ተቋማትን እና መሰረተ ልማቶችን ሲያወድም ምንም ያላሉት የድርጅቱ ዋና ዳይሬክተር የሰብዓዊ እርዳታን ምክንያት በማድረግ የኢትዮጵያን መንግስት ለማጥቃት ዘመቻ ከፍተዋል ብሏል።

የልዩ መልእክተኛው ጽህፈት ቤት ግለሰቡ የሚመሩትን ተቋም ኢትዮጵያን ለመጉዳት እየተጠቀሙበት መሆኑን ገልጾ ለዚህ ተግባሩ ገለልተኛ ምርመራ እንዲደረግም ጠይቋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም