ሕወሓት እርዳታን ለወታደራዊ አላማ የመጠቀም አደገኛ አካሄድ ፍጹም ተቀባይነት የሌለው ነው - ሴናተር ማርክ ዋርነር

498

ነሐሴ 25 ቀን 2014 (ኢዜአ) “ሕወሓት እርዳታን ለወታደራዊ አላማ የመጠቀም አደገኛ አካሄድ ፍጹም ተቀባይነት የሌለው ድርጊት ነው” ሲሉ የአሜሪካ የሴኔት የደህንነት ጉዳዮች ሰብሳቢ ማርክ ዋርነር ገለጹ።

ግጭቶችን በማቆም ወደ ሰላማዊ አማራጭ መመለስ ያስፈልጋል ብለዋል።

የኢትዮጵያ መንግስት ለሰላም አማራጭ ያቋቋመው ቡድን እንዲሁም በሰብአዊ ተኩስ አቁም አማካኝነት ተስፋ ሰጪ ለውጦች መታየታቸውንና የሰብአዊ እርዳታ ተደራሽነት ከፍተኛ ለውጥ መታየቱን ማርክ ዋርነር በትዊተር ገጻቸው ባሰፈሩት መረጃ ገልጸዋል።

ይሁንና በቅርቡ የተጀመረው ዳግም ግጭት እጅጉን እንዳሳሰባቸው ተናግረዋል።

በዚህ ረገድም ሕወሓት ነዳጅ በመዝረፍ እርዳታን ለወታደራዊ አላማ የመጠቀም አካሄድ አደገኛና ተቀባይነት የሌለው ድርጊት ነው ብለዋል።

በአስቸጋሪ ሁኔታ ለሚገኙ ዜጎች እርዳታና መሰረታዊ አገልግሎቶች እንዳይደርሳቸው የማገድ ወይም የማስተጓጎል የትኛውም አይነት ድርጊት ተቀባይነት የለውም ነው ያሉት ሴናተሩ።

አሜሪካ ለኢትዮጵያ የምታደርገው የሰብአዊና ልማት ድጋፍ እንዲያድግ በተደጋጋሚ ጊዜ እየሞገትኩ ነው ያሉት ሴናተሩ፤የአሁኑ ግጭት የተጀመሩ አበረታች ስራዎችን ስጋት ውስጥ የሚከትና የኢትዮጵያን ሕዝብ ላልተገባ ችግር የሚዳርግ መሆኑን አመልክተዋል።

የሚመለከታቸው አካላት ግጭቶችን በማቆም የሰብአዊ እርዳታ ተደራሽነት እንዲያድግና ግጭቱ በዘላቂነት እንዲቆም ጥረት እንዲያደርጉ ሴናተር ዋርነር ጥሪ አቅርበዋል።

የኢትዮጵያ መንግስት ያሳለፈው የሰብአዊ ተኩስ አቁም ውሳኔ ነሐሴ 18 ቀን 2014 ዓ.ም በአሸባሪው ህወሃት ተጥሶ የሰላም አማራጭ ሂደቱ አደጋ ላይ መውደቁ ይታወቃል።

ሴናተር ማርክ ዋርነር ከእ.አ.አ 2008 ጀምሮ በሴናተርነት በማገልገል ላይ ይገኛሉ።

የ67 ዓመቱ ሴናተር ከእ.አ.አ ጥር ወር 2021 አንስቶ ደግሞ የሴኔቱ የደህንነት ጉዳዮች ኮሚቴ ሰብሳቢ ሆነው በመስራት ላይ ናቸው።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም