የአዲስ አበባ ባህል፣ ኪነ-ጥበብና ቱሪዝም ቢሮ አዲስ ድረ-ገጽ ይፋ አደረገ - ኢዜአ አማርኛ
የአዲስ አበባ ባህል፣ ኪነ-ጥበብና ቱሪዝም ቢሮ አዲስ ድረ-ገጽ ይፋ አደረገ
አዲስ አበባ ሰኔ 28 ቀን 2014 (ኢዜአ) የአዲስ አበባ ባህል፣ ኪነ-ጥበብና ቱሪዝም ቢሮ በመዲናዋ ያሉ የቱሪስት መዳረሻዎችን የሚያስተዋውቅና መረጃ የሚሰጥ ድረ-ገጽ ይፋ አደረገ።
ቢሮው ድረ-ገጹን ያስመረቀው ከአዲስ አበባ ቴክኒክ ሙያ ሥልጠናና ቴክኖሎጂ ልማት ቢሮ ጋር በመተባበር ነው።
ድረ-ገጹ በአማርኛና በእንግሊዘኛ ቋንቋዎች የተዘጋጀ ሲሆን፤ በቀጣይ በሌሎች የአገር ውስጥ እና ዓለም አቀፍ ቋንቋዎች አገልግሎት መስጠት እንደሚጀምር ነው የተገለጸው።
ድረ-ገጹ በከተማዋ ካሉት የቱሪስት መዳረሻዎች፣ ሙዚየሞች፣ ሐውልቶች፣ ፓርኮች ቴአትር ቤቶች በተጨማሪ አጠቃላይ ተግባራቱንም የሚያስተዋውቅበትና መረጃ የሚሰጥበት እንደሆነም ተጠቁሟል።
የቢሮ ኃላፊ ዶክተር ሂሩት ካሣው፤ የድረ-ገጹ ሥራ ላይ መዋል የተለያዩ መረጃዎችን በአንድ ጊዜ ተደራሽ ለማድረግ ያግዛል ብለዋል።
የመረጃዎቹም ተደራሽነት በመዲናዋ ብቻ እንዳይወሰንና በሀገር አቀፍና ዓለም አቀፍ ደረጃ እንዲዳረስ ዓይነተኛ ሚና እንዳለው ገልጸዋል።
ድረገፁ እንደፌስቡክ ፣ ቲውተር ፣ ቴሌግራም ፣ ኢንስታግራም ካሉት ማኅበራዊ ድረገፆች ጋር የተሳሳረ እንደሆነም ተናግረዋል።
ድረ-ገጹ ከኅብረተሰቡ የሚመጡ አስተያየቶችን መቀበልና ሥራ ላይ ማዋልን ጨምሮ አገልግሎት ፈላጊዎች ማሟላት በሚገባቸው ጉዳዩች ላይ ግልጽ የሆነ መረጃ የሚቀመጥበት እንደሆነም አንስተዋል።
የቢሮው የመረጃ ግንኙነት አስተባባሪ አቶ ቴዎድሮስ እሸቱ፤ ድረ-ገጹ ከዚህ በፊት ያልተካተተውን የኪነ-ጥበብ ዘርፍ አቅፎ መያዙን ጠቁመዋል።
ከወቅቱ ቴክኖሎጂ ጋር የሚሄድ በመሆኑም ነባር መረጃዎችን ለማሻሻልና አዳዲስ መረጃዎችን በፍጥነት ለማድረስ ይረዳል ነው ያሉት።
ድረ-ገጹን ያበለፀጉት የአዲስ አበባ ቴክኒክ ሙያ ሥልጠናና ቴክኖሎጂ ልማት ቢሮ የሶፍትዌር ኢንጂነሪንግ ባለሙያዎች አብረሃም ረታ እና አብዱልከሪም ሰዒድ እንደገለፁት፤ ድረ-ገጹ በየጊዜው መሻሻል እንዲችል ሆኖ የተዘጋጀ ነው።
በመሆኑም በቀጣይ የመዲናዋ የትራንስፖርት፣ የቪዛ አገልግሎት፣ የአየር ንብረት ሁኔታና ሌሎችም መረጃዎችን በማካተት ድረ-ገጹን አመቺ በሆነ መልኩ ለማበልጸግ መታሰቡን ጠቁመዋል።