ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ የዘንድሮውን የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር በይፋ አስጀመሩ

176

ሰኔ 14 ቀን 2014 (ኢዜአ) ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ የዘንድሮውን የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር ዛሬ በጉለሌ ዕፅዋት ማዕከል በይፋ አስጀምረዋል።

በማስጀመሪያ መርሃ-ግብሩ የኢትዮጵያ የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ፣ የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀመንበር ሙሳ ፋኪ ማሃመት፣ የክልል ርዕሳነ መስተዳድሮች፣ የፌደራልና የክልል መንግሥታት ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች፣ አምባሳደሮች፣ የሃይማኖት አባቶች ተገኝተዋል። 

"አሻራችን ለትውልዳችን" በሚል መሪ ሀሳብ በሚካሄደው የዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር 6 ቢሊዮን ችግኞችን ለመትከል ታቅዷል።

ኢትዮጵያ ከ2011 ዓ.ም ጀምሮ በተከታታይ አራት ዓመታት 20 ቢሊዮን ችግኞችን ለመትከል ግብ ይዛ እየሠራች ትገኛለች።

ዘንድሮ የሚካሄደው የ6 ቢሊዮን ችግኞች ተከላ በእቅዱ መሠረት ከተከናወነ በአራት ዓመት የተያዘው 20 ቢሊዮን ችግኞች የመትከል ግብ ከእቅድ በላይ ይሳካል።

ባለፉት አራት ዓመታት የተተከሉ ችግኞች አማካይ የጽድቀት ምጣኔ ከ80 በመቶ በላይ መሆኑ የተነገረ ሲሆን በዚህ ዓመት እንደ አየር ንብረቱ ተስማሚ የሆነ ችግኝ ለመትከል በትኩረት እየተሰራ ነው ተብሏል።

በዚህም ለደን ዛፍ፣ ለጥምር ደን እርሻ፣ ለምግብ የሚያገለግሉ፣ ለመኖ የሚውሉ እና የተለያዩ ሀገር በቀል ችግኞች ለተከላ መዘጋጀታቸው ታውቋል።

ኢትዮጵያን እናልማ፣ እንገንባ፣ እንዘጋጅ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም