ለተዝካር መደገሻ ሊውል የነበረ 1 ሚሊየን ብር ለዘማች ቤተሰቦችና ለህልውና ዘመቻ ድጋፍ ተደረገ

58

ጎንደር፤ ታህሳስ 28/2014 (ኢዜአ ) አቶ ነብዩ ተገኘ የተባሉ ግለሰብና ቤተሰቦቻቸው ለወላጅ እናታቸው ተዝካር መደገሻ ሊያውሉት የነበረን 1 ሚሊዮን ብር ለህልውና ዘመቻውና በጎንደር ከተማ ለሚገኙ የዘማች ቤተሰቦች ለበዓል መዋያ በስጦታ አበረከቱ፡፡

ነዋሪነታቸውን በአዲስ አበባ ያደረጉት  አቶ ነብዩ ተገኘ እና ቤተሰቦቻው ድጋፉን ያደረጉት ጥር 7 ቀን 2014 ዓም ለወላጅ እናታቸው እማሆይ ተናኘወርቅ በላቸው የተስካር ድግስ  ወጪ ለማድረግ ያዘጋጁትን ገንዘብ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

"ሀገር በችግር ላይ ሆና ህዝቡ ለሀገሩ ህልውና ውድ ህይወቱን ጭምር በመስጠት መስዋእትነት እየከፈለ ባለበት በዚህ ወቅት ድግስ መደገስ አያስፈልግም" ሲሉ ተናግረዋል።

ለድግስ ሊያውሉት ከነበረ 1 ሚሊዮን ብር ውስጥ በጎንደር ከተማ ለሚገኙ 115 የዘማች ቤተሰቦች  ለገና በዓል መዋያ ለእያንዳንዳቸው 5 ሺህ  ብር በአጠቃላይ 575 ሺህ ብር እንዲሰጥ መደረጉን አስረድተዋል።

ቀሪውን ገንዘብ ደግሞ በህልውና ዘመቻው ለሚዋደቁ የጸጥታ አካላት በድጋፍ ማበርከታቸውን አስታውቀዋል።

በገንዘብ ስጦታ ርክክብ ሥነ-ሥርዓቱ  ላይ የተገኙት የጎንደር ከተማ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ዘውዱ ማለደ  በህውልና ዘመቻው ህዝቡ ያሳየው አንድነትና መደጋገፍ የአሸባሪው ህወሓትን ሀገር የማፍረስ ህልም በከንቱ ማስቀረቱን ተናግረዋል ።

"መረዳዳትና መደጋገፍ የኢትጵያዊያን በጎ እሴቶች መገለጫ ናቸው" ሲሉም ገልጸዋል።

አቶ ነብዩና ቤተሰቦቻቸው ያደረጉት ሰብአዊነት የተላበሰ በጎ ምግባር በአርዓያነቱ የሚጠቀስ መሆኑን የገለጹት አቶ ዘውዱ፤  ግለሰቦቹ  ላደረጉት ድጋፍ በከተማ አስተዳዳሩ ስም አመስግነዋል፡፡

'ህዝቡ  ለዘማች ቤተሰቦች እያደረገ ያለው ያልተቋረጠ ድጋፍ ለወገን ደራሽ ወገን ነው የሚለውን ኢትዮጵያዊ በጎነት በተግባር ያረጋጋጠ ነው'' ያሉት ደግሞ ልጃቸውን ወደ ግንባር የላኩት አቶ መኮንን መብራቱ የተባሉ የከተማው ነዋሪ ናቸው፡፡

በዛሬው እለት ለገና በአል መዋያ 5 ሺህ  ብር እንደተሰጣቸው ጠቁመው፤ በግዳጅ ላይ የሚገኘውን ልጃቸውን በማሰብ በአዓሉን በደስታ እንደሚያሳልፉ ተናግረዋል፡፡

ባለቤታቸው አሸባሪውን ህወሓት ለመፋለም ወደ ግንባር ቢዘምቱም የህዝቡ ድጋፍ ለአንድ አፍታም ቢሆን እንዳልተቋረጠባቸው የገለጹት ደግሞ ወይዘሮ አስካል ገብሩ ናቸው፡፡

ለተደረገላቸው ድጋፍ ያመሰገኑት ወይዘሮ አስካለ፤ ድጋፉን ላደረጉት ቤተሰቦች ፈጣሪ የሟች ወላጅ እናታቸውን ህይወት በአጸደ ገነት እንዲያኖርላቸው መልካም ምኞታቸውን ገልጸዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም