ከአንበሳ ግቢ አምልጣ የወጣች ጦጣ  በሰዎች ላይ ጉዳት አደረሰች

167
ነሀሴ 21/2010 ከአንበሳ ግቢ መዝናኛ ፓርክ አምልጣ ወጥታ በአካባቢው ሰዎች ላይ ጉዳት ያደረሰችዋ ጦጣ እስከ አሁን አለመያዟ እንዳሳሰባቸው የአካባቢው ነዋሪዎች ተናገሩ፡፡ የአንበሳ ግቢ መዝናኛ ፓርክ ጦጣዋን ለመያዝ ጥረት እያደረገ  መሆኑን አስታውቋል፡፡ ተማሪ ነቢዩ ኢሳኢያስ በአራዳ ክፍለ ከተማ የወረዳ አንድ ነዋሪ ነው፡፡ ነሐሴ 19 ቀን 2010 ዓ.ም ከጠዋቱ ሶስት ሰዓት አካባቢ በአቅራቢያው ወዳለ ሱቅ በማምራት ላይ ሳለ ጦጣዋ ከኋላው ዘላ እግሩን ነክሳው ጉዳት አድርሳበት አምልጣለች፡፡ በግል ስራ እንደሚተዳደር የነገረን ወጣት ድልነሳው ይገዙ ደግሞ ወደ ስራ ለመሄድ ፊቱ በመታጠብ ላይ ሳለ ይሕችው ጦጣ ከኋላው በኩል እግሩን ነክሳ ከፍተኛ የሚባል ጉዳት አድርሳበታለች፡፡ በጦጣዋ ከፍተኛ ጉዳት በማስተናገዱ መንቀሳቀስ  እንደማይችል የገለጸልን ወጣት ድልነሳው  በመሃል ከተማ ከሚገኝ ፓርክ እንስሳት በዚህ መልኩ ማምለጥ መቻላቸው አሳሳቢ መሆኑን ገልጿል፡፡ የልጆችን ጩኸት ሰምቶ ወደ ውጪ በወጣበት ጊዜ ከጦጣዋ ጋር ፊት ለፊት የተፋጠጠው ህጻን አቤኔዘር አጥናፉ ራሱን ለማዳን  የግቢውን በር ቢዘጋም በአጥር ዘልላ ታፋውን  እንደነከሰቸው ነው የተናገረው፡፡ የወላጅ አቤኔዘር እናት ወይዘሮ ፈትለወርቅ ተክሌ ለኢዜአ እንዳሉት ፓርኩ የእንስሳት ማቆያ እንደመሆኑ መጠን በቂ ጥበቃ ሊደረግለት ይገባ ነበር፡፡ የጦጣዋ አለመያዝ አሁንም ድረስ ስጋት እንደፈጠረባቸው ተናግረዋል፡፡ የስድስት ዓመት ህጻን ልጃቸው በጦጣዋ ጉዳት እንደረሰበት የተናገሩት ወይዘሮ  አጃይባ ዋባ በበኩላቸው ልጃቸውን ለማሳከም 3 ሺህ 500 ብር ማውጣታቸውን ገልጸዋል፡፡ ሌላዋ የአካባቢው ነዋሪ ወይዘሪት ሶፊያ አወል እንዳለችው ሰዎች ላይ ከደረሰው ጉዳት በላይ የጦጣዋ ጤንነት አሳስቧታል፡፡ ተቋሙ መሰል እንስሳት አምልጠው ከዚህም የባሰ ጉዳት እንዳያደርሱ የጥበቃ ስራውን ሊያጠናክር እንደሚገባም ጠቁማለች፡፡ የአንበሳ ግቢ መዝናኛ ፓርክ አስተባባሪ አቶ ይርጋለም አያሌው ጦጣዋ  የማደሪያዋን ኮርኔስ ገንጥላ  ማምለጧን ገልጸው ጦጣዋን ለመያዝ ጥረት ቢደረግም አለመሳካቱን አምነዋል፡፡ አሁንም ዳርት /ማደንዘዣ/ በመጠቀም ጦጣዋን ለመያዝ ጥረት እየተደረገ መሆኑን ያብራሩት አስተባባሪው ካልተሳካ ሌሎች አማራጮችን እንደሚጠቀሙ አረጋግጠዋል፡፡ ፓርኩ በሚቀርብለት ደረሰኝ መሰረት ተጎጂዎች ያወጡትን ወጪ ለመክፈል ዝግጁ መሆኑንም አስተባባሪው ተናግረዋል፡፡
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም