'ዩናይትድ ራሺያ' ፓርቲ ከብልጽግና ፓርቲ ጋር ትብብሩን ያጠናክራል

89

ታህሳስ 15/2014 /ኢዜአ/ 'ዩናይትድ ራሺያ' ፓርቲ ከብልጽግና ፓርቲ ጋር ትብብሩን ለማጠናከር ቁርጠኛ መሆኑን በኢትዮጵያ የራሺያ አምባሳደር ኤቭጌኒ ቴሬክሂን ተናገሩ።

አምባሳደሩ ይህን የተናገሩት 20ኛው የ'ዩናይትድ ራሺያ' ፓርቲ ምስረታ በአዲስ አበባ የራሺያ የባህልና ሳይንስ ማዕከል ሲታሰብ ነው።

ሁለቱ ገዥ ፓርቲዎች የሚያደርጉት ትብብር በሁለቱ አገራት መካከል ያለውን የጋራ መግባባትና መተማመን ያጠናክራልም ብለዋል።

ፓርቲዎቹ በኢትዮጵያና በራሺያ ያሉ ዋና እና ወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ለመመካከርና መረጃ ለመለዋወጥ መስማማታቸውንም አንስተዋል አምበሳደሩ።

ይህ ብቻ ሳይሆን 'ዩናይትድ ራሺያ' ፓርቲ ከብልጽግና ፓርቲ ጋር ትብብሩን ለማጠናከር ቁርጠኛ መሆኑን አክለዋል።

እንደ አምባሳደሩ ገለጻ፣ ሁለቱ ፓርቲዎች በዓለም ዓቀፍ ጉዳዮች ላይ ሀሳብ መለዋወጥ፣ የልምድ ልውውጦችን ማድረግ፣ የፓርቲ ግንባታና የፓርላማ እንቅስቃሴ ላይም ጠቃሚ ውይይቶችን ማድረግ አስፈላጊ መሆኑን ያምናል።

የብልጽግና ፓርቲ ዋና ጸሃፊ አደም ፋራህ፤ ዩናይትድ ራሺያ ፓርቲ ለ20ኛ ዓመት ክብር በዓል መድረሱን አስመልክተው ለፓርቲው አባላትና ለመላው የሩሲያ ህዝብ እንኳን ደስ ያላችሁ ብለዋል።

ፓርቲው የሩሲያን ሕዝብ ማሕበረ-ምጣኔ ኃብታዊና ፖለቲካዊ ተግዳሮቶችን ለመፍታት የወሰደው አመራርነት የሚደነቅ መሆኑንም አቶ አደም ጠቁመዋል።

የብልጽግና ፓርቲም ከ'ዩናይትድ ራሺያ' ፓርቲ የስኬት መንገዶች ብዙ ነገሮችን ተሞክሮ ይጋራል ነው ያሉት።

ኢትዮጵያና ሩሲያ ከምዕተ ዓመት በላይ የዘለቀ የኢኮኖሚ፣ የፖለቲካ፣ የባህል፣ የሕዝብ ለሕዝብና ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት እንዳላቸውም አስታውሰዋል።

'ዩናይትድ ራሺያ' ፓርቲና የሩሲያ መንግስት እያደረጉ ላሉት ቀጣይነት ያለው ድጋፍም አቶ አደም ምስጋና አቅርበዋል።

በተለይም ሩሲያ በመንግስታቱ ድርጅት የጸጥታው ምክር ቤት ኢትዮጵያን በሚመለከት እያደረገች ያለው እውነትን የተከተለ ድጋፍ ታሪክ አይረሳውም ብለዋል።

ይህም አመላካችነቱ ሩሲያ በአገራት ሉዓላዊነት ጉዳይ ላይ እውነታንና መርህን መሰረት ያደረገ አካሄድ ያላት መሆኗን የሚያረጋግጥ ነው ብለዋል።

ለኢትዮጵያ እድገትና ለህዝቦች አብሮነት እየሰራ ያለው ብልጽግና ፓርቲ ከዩናይትድ ራሺያ ፓርቲ ጋር ግንኙነቱን ይበልጥ ለማጠናከር ቁርጠኛ መሆኑን አቶ አደም አረጋግጠዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም