የአውሮፓ ህብረት ስለኢትዮጵያ ያቀረበው የውሳኔ ሃሳብ ተቀባይነት የለውም-ፊሊፒንስ

99

ታህሳስ 08 ቀን 2014 (ኢዜአ) የአውሮፓ ህብረት በትግራይ ክልል የሰብአዊ መብቶች ጥሰት ተፈጽሟል በሚል ሊነጋገርበት ቀጠሮ የያዘለት የውሳኔ ሃሳብ በፍጹም ተቀባይነት እንደሌለው በጄኔቫ የሚገኘው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የፊሊፒንስ ቋሚ መልእክተኛ ኤቫን ጋርሽያ ገለጹ።

የፊሊፒንስ የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት ሃላፊ ቴዮዶር ሎክሲን በኢትዮጵያ ተፈጽሟል የተባለውን የሰብአዊ መብቶች ጥሰት ለማጣራት የሚቋቋመው አለምአቀፍ የሰብአዊ መብቶች ባለሙያዎች ኮሚሽን ዋነኛ አላማ የሰብአዊ መብቶች ጥበቃ ሳይሆን በሃገራት የውስጥ ጉዳይ ጣልቃ መግባትና ሉአላዊነትን የመጋፋት ፍላጎት አድርገን እንወስደዋለን ብለዋል።የዚህ ሃሳብ አቀንቃኞች ፍላጎታቸው ጣልቃ ለመግባት ከመሻት የመነጨ መሆኑን በአጽንኦት ተናግረዋል።

አክለውም ሀላፊው “የኢትዮጵያ መንግስት ችግሩን በመረዳት የማስተካከያ እርምጃዎችን እንደሚወስድና ተጠያቂነትን ለማስፈን እየሰራ ባለበት በዚህ ወቅት ተመሳሳይ አጀንዳ አንስቶ የውሳኔ ሃሳብ ለማምጣት የሚደረገው ጥረት ሉአላዊነትን ከመጣስ ውጪ ምን ሊሆን ይችላል? ምን አዲስ ነገርስ ያመጣሉ?” ሲሉም ጠይቀዋል።

“የውሳኔ ሃሳቡ ለጉዳዩ አቀንቃኞች የተሳሳተ ስራ ትክክል የመሆን ስሜት ከመፍጠር ባሻገር የሚያመጣው ለውጥ የለም” ያሉት ሃላፊው “እ.ኤ.አ በ2019 ፊሊፒንስም በእጽ አዘዋዋሪዎች ላይ ተፈጸሙ በተባሉ የሰብአዊ መብቶች ጥሰት ስሟ በአስመሳዮች ሲጠፋ ነበር” ሲሉ መናገራቸውን ኒውስ ኤቢኤስ በድረገጹ አስነብቧል።

ሉአላዊነትን ለመጣስ በማሰብ ጉዳዩን ከተገቢው በላይ በመለጠጥ የሚያራግቡ ሃገራት ራሳቸው በርካታ የሰብአዊ መብቶች ጥሰቶች የሚፈጸሙባቸውና ለችግሮቻቸው መፍትሄ ያላስቀመጡ መሆናቸውን ገልጸው የግል ፍላጎታቸውን ለማስጠበቅና የራሳቸውን ጥፋቶች ለመሸፋፈን የሰብአዊ መብቶች ምክርቤቱን ከመጠቀም ሊቆጠቡ እንደሚገባም ተናግረዋል።

ተመሳሳይ ጉዳዮች እየተነሱ የሚወድቁበትና ያለ ፍርድ ሂደት ሃገራት ላይ ውሳኔ የሚሰጥበት፣ የሃገራት ሉአላዊነት የሚደፈርበት ብሎም ለውይይት በር የሚዘጋው ይሄ አይነቱ አካሄድ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሰብአዊ መብቶች ምክር ቤቱን አቅም የሚያዳክም ነውም ብለዋል።

በመሆኑም ይህ አካሄድ ካልተስተካከለ በስብሰባው ላይ የምትታደምው ፊሊፒንስ በተቃውሞ እንደምትወጣ ከወዲሁ እወቁት ሲሉ ማስጠንቀቃቸውን መረጃው አስታውሷል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም