“ከዚህ በኋላ የትኛውም ጠላት ኢትዮጵያን ለመድፈር የሚሞክር አይመስለኝም”

69

ህዳር 23 /2014/ኢዜአ/ “ከዚህ በኋላ የትኛውም ጠላት ኢትዮጵያን ለመድፈር የሚሞክር አይመስለኝም” ሲሉ በጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት የዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታ ማዕከል አስተባባሪ ዶክተር ቢቂላ ሁሪሳ ተናገሩ።

ከኢዜአ ጋር በወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ቆይታ ያደረጉት ዶክተር ቢቂላ፤ በህዝብ ሃይል ከስልጣን ተገፍቶ የወጣው አሸባሪው ህወሓት ከውጭ ሃይሎች ጋር በመቀናጀት ኢትዮጵያን ለማፍረስ ፕሮጀክት ቀርፆ የሰራ መሆኑን ገልጸዋል።

የሽብር ቡድኑ "እኔ ያልመራኋት ኢትዮጵያ መፍረስ አለባት" ብሎ በማቀድ ከህፃናት እስከ አዛውንት ለዘመቻ አሰልፎ ኢትዮጵያን አፈርሳለሁ ብሎ እየሰራ ይገኛል።

በኢትዮጵያ ላይ ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ፍላጎቸውን ባልተገባ ሁኔታ ለመጫን የሚሹ የውጭ ሃይሎች ደግሞ የአሸባሪውን እኩይ አላማ ደግፈው ቆመዋል።

ኢትዮጵያ በትክክለኛ የለውጥ ጎዳና ላይ መሆኗን የጠቀሱት ዶክተር ቢቄላ፤ ክብሯንና ነፃነቷን አስጠብቃ በመዝለቅ በፓን አፍሪካኒዝም የአፍሪካ የነፃነት ትግል ፊት አውራሪ ሆና ትቀጥላለች ብለዋል።

በኢትዮጵያ ባለፉት 3 ዓመታት የኢትዮጵያ ትክክለኛ የለውጥ ሂደትና የብልጽግና ራእይ ያልተመቻቸው የውስጥ ካሃዲዎችና የውጭ ሃይሎች ሊያደናቅፏት በጥረት ላይ ይገኛሉ ነው ያሉት።

ሆኖም ኢትዮጵያዊያን ለአገራቸው ክብርና ሉአላዊነት ጠላቶችን በጋራ ክንዳቸው በመመከት አይበገሬነታቸውን በተግባር እያሳዩ መሆኑን ዶክተር ቢቄላ ገልጸዋል።

የኢትዮጵያ የቁርጥ ቀን ልጆች ለአገራቸው እያሳዩት ያለው ጀግንነትና የድል ግስጋሴ "ከዚህ በኋላ የትኛውም ጠላት ኢትዮጵያን ለመድፈር የሚሞክር አይመስለኝም" ሲሉም ዶክተር ቢቂላ ተናግረዋል።

በመሆኑም በኢትዮጵያ ላይ የሚያሴሩ ጣላቶች ኢትዮጵያ የማትደፈር የበርካታ ጀግኖች አገር መሆኗን ሊገነዘቡ ይገባል ነው ያሉት።

ኢትዮጵያ የገጠማትን ወቅታዊ ፈተና በጀግኖች ልጆቿ የተባበረ ክንድ ታልፈዋለች፤ በፓን አፍሪካኒዝም የአፍሪካ የነፃነት ትግልም ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም