ግብጽ የውሃ ጉዳይ የጸጥታው ምክር ቤት አጀንዳ እንዲሆን ያቀረበችው ጥያቄ ውድቅ ተደረገ

70

መስከረም 6/2014 (ኢዜአ) ግብጽ የህዳሴው ግድብ ከፍተኛ የውሃ እጥረት የሚያስከትል በመሆኑ አለምአቀፍ የሰላምና መረጋጋት ችግር መንስኤ ነው በማለት የጸጥታው ምክር ቤት አጀንዳ እንዲሆን ያቀረበችው ሀሳብ ተቀባይነት እንዳላገኘ ዘናሽናል ኒውስ ዘግቧል።

ግብጽ በተደጋጋሚ የህዳሴው ግድብ በሀገሪቱ ብሔራዊ ጥቅም ላይ አደጋ እንደደቀነባት ስሞታ ስታቀርብ ከመቆየቷም ባሻገር ግድቡን ለማፍረስ ወታደራዊ እርምጃን ጨምሮ ማንኛውንም አማራጭ እንደምትጠቀም መግለጿ የሚታወስ ነው።

በአንፃሩ ኢትዮጵያ ግድቡ በታችኞቹ ተፋሰስ ሀገራት ላይ ጉዳት እንደማያደርስ ብዙ ጊዜ አሳውቃለች።   

ግብጽ የጸጥታው ምክር ቤት የውሃ ጉዳይ አጀንዳው እንዲያደርግና የህዳሴው ግድብም ዓለም አቀፍ አጀንዳ እንዲሆን ጥያቄ ብታቀርብም ምክር ቤቱ ጉዳዩ የልማት አጀንዳ እንጂ የሰላምና ጸጥታ አለመሆኑን በማስገንዘብ ጥያቄውን ውድቅ አድርጓል።

ሀገሪቱ ባሳለፈነው አንድ ዓመት ብቻ በተደጋጋሚ ጉዳዩን ወደ ጸጥታው ምክር ቤት ለመውሰድ ከፍተኛ ግፊት ማድረጓ የሚታወስ ነው።

የጸጥታው ምክር ቤት የግብጽን ጥያቄ ውድቅ በማድረግ ሶስቱ ሃገራት በአፍሪካ ህብረት መሪነት ገንቢና ትብብር በተሞላበት መንገድ በአፋጣኝ ወደ ድርድሩ እንዲመለሱ አሳሰቧል።

በተባበሩት መንግስታት የኢትዮጵያ አምባሳደር ታዬ አጽቀስላሴ ምክር ቤቱ አለምአቀፍ ሰላምና መረጋጋትን የተመለከቱ ጉዳዮችን ብቻ የማየት ስልጣን እንዳለው በመጥቀስ፤ ጉዳዩ የሚቋጨው በሶስትዮሽ ድርድር ብቻ በመሆኑ ግብጽና ሱዳን ወደ ድርድሩ ፈጥነው እንዲመለሱ መጠየቃቸውንም ዘገባው አመልክቷል።    

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም