የኢትዮጵያ ቀይ መስቀል ማኅበር በደባርቅ ከተማ ለሚገኙ ተፈናቃዮች ድጋፍ አደረገ

85

ነሐሴ 21 ቀን 2013 (ኢዜአ) የኢትዮጵያ ቀይ መስቀል ማኅበር አሸባሪው የህወሓት ቡድን በከፈተው ጦርነት ምክንያት ከመኖሪያቸው ተፈናቅለው በደባርቅ ከተማ ለሚገኙ ዜጎች ድጋፍ አደረገ።

የማኅበሩ የሰሜን ጎንደር ቅርንጫፍ ፅህፈት ቤት ኃላፊ አቶ አታለል ታረቀኝ የተደረገው ድጋፍ ለእናቶችና ህፃናት የሚሆን አልሚ ምግብና የንፅህና መጠበቂያ ቁሳቁስ መሆኑን ለኢዜአ ገልፀዋል።

ድጋፉ ከተፈናቃዮቹ ቁጥር አንፃር በቂ አለመሆኑን ገልጸው፤ ከሚቀጥለው ሣምንት ጀምሮ ከዓለም አቀፉ ቀይ መስቀል ማኅበር ጋር በመተባበር የተሟላ  ድጋፍ ለማድረግ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል።

ከኢትዮጵያ ቀይ መስቀል ማኅበር ዋና መስሪያ ቤት ተጨማሪ ድጋፍ ለማምጣት በሂደት ላይ መሆኑን የገለጹት ኃላፊው፤ በሰሜን ጎንደር ዞን ከሚገኙ 15 ሺህ ተፈናቃዮች ከ50 በመቶ በላይ ለሚሆኑት ድጋፍ ለማድረግ ዝግጅት መኖሩን ጠቁመዋል።

ማኅበሩ ሁለት ሺህ ለሚሆኑ ተፈናቃዮች በሁለት ዙር ድጋፍ ማድረጉንም አቶ አታለል ገልጸዋል።

በደባርቅ ከተማ የሚገኙት ተፈናቃዮች ከአዲ አርቃይ፣ ጠለምትና ማይጠብሪ ወረዳዎች የመጡ ናቸው።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም