በአሜሪካ የአፍሪካ ኮርፖሬት ምክር ቤት ከኢትዮጵያ ጋር ያለውን ትስስር ማጠናከር እንደሚፈልግ አስታወቀ

155
አዲስ አበባ ሀምሌ 3/2010 በአሜሪካ የአፍሪካ ኮርፖሬት ምክር ቤት ከኢትዮጵያ ጋር ያለውን ትስስር ማጠናከር እንደሚፈልግ አስታወቀ። በአሜሪካ የኢትዮጵያ አምባሳደር አቶ ካሳ ተክለብርሃን በአሜሪካ የአፍሪካ ኮርፖሬት ምክር ቤት ፕሬዝዳንት ፍሎሪዘል ሊዘር ጋር መወያየታቸውን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ጽህፈት ቤት አስታውቋል። በውይይቱ ፣ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ በአሜሪካ ያደረጉትን ስኬታማ ጉብኝት ተከትሎ የተፈጠሩት ምቹ ሁኔታዎች እንዲሁም በኢትዮጵያ ውስጥ እየተካሄዱ ያሉ የፖለቲካና የኢኮኖሚ ማሻሻያዎች ፣ በአሜሪካና በኢትዮጵያ መካከል ያለውን የኢኮኖሚ ግንኙነት ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋገር መልካም አጋጣሚ እንደፈጠረ ተወስቷል፡። ባለስልጣናቱ በኢትዮጵያና በአሜሪካ መካከል ያሉት የንግድና የኢንቨስትመንት ትስስሮች በሚጠናከሩባቸው ሁኔታዎች ላይም መክረዋል። በአሜሪካ የአፍሪካ ኮርፖሬት ምክር ቤት ፕሬዝዳንት ፍሎሪዘል ሊዘር ምክር ቤቱ ከኢትዮጵያ ጋር ያለውን ትስስር ማጠናከር እንደሚፈልግ ገልጸዋል። ምክር ቤቱ በርካታ ከአነስተኛና መካከለኛ እስከ ድንበር ተሻጋሪ ኩባንያዎችን ያቀፈ የአሜሪካ ግንባር ቀደም የቢዝነስ ማህበር መሆኑን ከጽህፈት ቤቱ የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም