በተጠናቀቀው የ2013 በጀት ዓመት ከወጪ ንግድ 3 ነጥብ 62 ቢሊዮን ዶላር ገቢ መገኘቱን የንግድና ኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ገለጸ - ኢዜአ አማርኛ
በተጠናቀቀው የ2013 በጀት ዓመት ከወጪ ንግድ 3 ነጥብ 62 ቢሊዮን ዶላር ገቢ መገኘቱን የንግድና ኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ገለጸ
ሐምሌ 16 2013 (ኢዜአ) በተጠናቀቀው የ2013 በጀት ዓመት ከወጪ ንግድ 3 ነጥብ 62 ቢሊዮን ዶላር ገቢ መገኘቱን የንግድና ኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ገለጸ።
ከአጠቃላይ ገቢው ግብርና 2 ነጥብ 47 ቢሊዮን ዶላር መሸፈኑም ተገልጿል።
የንግድና ኢንዱስትሪ የውጭ ንግድ ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ምስጋኑ አረጋ የ2013 በጀት ዓመት የወጪ ንግድ ገቢን አስመልክተው መግለጫ ሰጥተዋል።
በመግለጫቸው ከወጪ ንግድ የተገኘው 3 ነጥብ 62 ቢሊዮን የአሜሪካ ዶላር ገቢ የዕቅዱን 88 በመቶ ማሳካት እንደተቻለ እና የዕቅድ አፈጻጸም ከ2012 በጀት ዓመት ጋር ሲነጻጸር የ19 ነጥብ 5 በመቶ ወይም ከ592 ሚሊዮን ዶላር በላይ ብልጫ እንዳለው ተናግረዋል።
አምባሳደር ምስጋኑ አርጋ እንደገለፁት የግብርና ዘርፍ 2.47 ቢሊዮን የአሜሪካ ዶላር በማስመዝገብ ከአጠቃላይ የወጭ ንግድ ገቢው 68%፣ የማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ 390 ሚሊየን በማስመዝገብ የእቅዱን 67% ያስገኙ ሲሆን ፤ ከአጠቃላይ የወጭ ንግድ ገቢው 11%፣ የማዕድን ዘርፍ 668 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር ገቢ በማስመዝገብ የዕቅዱን 102% ከአጠቃላይ የወጭ ንግድ ገቢው 18% ድርሻ ሲኖራቸው 93 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር ገቢ ያስገኙ ናቸው
የአፈፃፀሙን ቀሪ 3% ድርሻ የሚይዙት የኤሌክትሪክና ኤሌክትሮኒክስ ምርቶች ናቸው ብለዋል፡፡
ከአጠቃላይ የወጭ ንግድ ገቢው 83% የገቢ ድርሻውን ያስመዘገቡ ምርቶች ቡና 25%፣ አበባ 13%፣ የቅባት እህሎች 9%፣ ጫት 11%፣ የጥራጥሬ ሰብሎች 6% እና ወርቅ 19% በመያዝ ከወጭ ንግዱ አጠቃላይ ገቢ 3 ቢሊዮን የአሜሪካ ዶላር ገቢ ተገኝቷል፡፡
አሜሪካ፣ አውሮፓ፣ ጃፓን፣ ሳዑዲ ዓረቢያ፣ ሲንጋፖር፣ እስራኤል እና ቻይና የወጨ የምርቶቹ መዳረሻ ሀገራት ናቸው፡