የግል ተቋማት እና ኩባንያዎች በአካባቢያቸው ያሉ የህብረተሰብ ክፍሎችን በማገዝ ማህበራዊ ኃላፊነታቸውን ሊወጡ ይገባል… ም/ከንቲባ አዳነች አቤቤ

66

ሚያዚያ 11 /2013 (ኢዜአ) በከተማዋ በተለያዩ ዘርፎች ተሰማርተው የሚገኙ የግል ተቋማት እና ኩባንያዎች በአካባቢያቸው ያሉ የህብረተሰብ ክፍሎችን በማገዝ ማህበራዊ ኃላፊነታቸውን በአግባቡ ሊወጡ እንደሚገባ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ ወ/ሮ አዳነች አቤቤ ገለፁ ።

ምክትል ከንቲባ ወ/ሮ አዳነች አቤቤ ከትምህርት ሚኒስትሩ ዶ/ር ኢኒጂነር ጌታሁን መኩሪያ ጋር ሲልክሮድ አጠቃላይ ሆስፒታል በዙሪያው ላሉት ነዋሪዎች በንጹሕ የመጠጥ ውሃ አቅርቦት ያደረገውን ድጋፍ ጎብኝተዋል።

በመርሐግብሩ ምክትል ከንቲባዋ እንደገለፁት የሲልክሮድ አጠቃላይ ሆስፒታል ማህበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ አስተዋፅኦ በማድረግ ያሳየውን ምሳሌነት በማንሳት አመስግነዋል።

በከተማዋ ውስጥ ያሉ ትልልቅ ተቋማትና ኩባንያዎች ማህበራዊ ሀላፊነታቸውን በመወጣት የሲልክ ሮድ አጠቃላይ ሆስፒታልን ተሞክሮ ሊተገብሩ እንደሚገባም ነው ወ/ሮ አዳነች የጠቆሙት ።

የሲልክ ሮድ አጠቃላይ ሆስፒታል ለማህበረሰቡ ነጻ የህክምና አገልግሎት ከመስጠት ጀምሮ በተለያዩ ተግባራት በማገዝ ማህበራዊ ኃላፊነቱ እየተወጣ መሆኑንና በቀጣይም አጠናክሮ እንደሚቀጥል የሆስፒታሉ ስራ አስኪያጅ ገልጸዋል ።

ሆስፒታሉ የከተማዋን የጤና ቱሪዝም መዳረሻነት ለማሳደግ በሚደረገው ጥረትም ተጨማሪ አለም አቀፍ የህክምና የልህቀት ማዕከል ለመገንባት እቅድ መያዙንም ስራ እስኪያጁ ተናግረዋል ።

በመርሐግብሩ ተጠቃሚ የሆኑ የህብረተሰብ ክፍሎች ምስጋና ማቅረባቸውን ከአዲስ አበባ ፕሬስ ሴክሬታሪ ጽ/ቤት ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።

1616

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም