የአድዋ ድል ቡድናዊና ግላዊ ፍላጎትን ሳይሆን አገራዊ ነገርን ማስቀደም እንደሚገባ አሳይቶናል ... ዶክተር ሂሩት ካሳው

65

አዲስ አበባ፤የካቲት 23/ 2013 (ኢዜአ) “የአድዋ ድል ቡድናዊና ግለሰባዊ ፍላጎትን ሳይሆን አገራዊ ነገርን ማስቀደም እንደሚገባ አሳይቶናል” ሲሉ የባህልና ቱሪዝም ሚኒስትር ዶክተር ሂሩት ካሳው አስታወቁ።

125ኛው የአድዋ ድል በዓል በርካታ ታዳሚዎች በተገኙበት በአዲስ አበባ ዳግማዊ ምኒሊክ አደባባይ በድምቀት እየተከበረ ይገኛል።

በዚህ ወቅት የባህልና ቱሪዝም ሚኒስትሯ ዶክተር ሂሩት “የአድዋ ድል ለቅኝ ገዢዎች አስደንጋጭና ታላቅ ፍርሃትን የፈጠረና ሽንፈትን በግላጭ ያሳየ ነው” ብለዋል።

“ኢትዮጵያውያን በወቅቱ የነበረውን ችግርና ሌሎች ነገሮች በመቋቋም በሙሉ ጀግንነትና ወኔ ድሉን ተጎናጽፈዋል፤ ይህም ለጥቁር ህዝቦች መነሻ ሆኖ ነጻነታቸውን እንዲቀዳጁ አድርጓቸዋል” ሲሉ ገልጸዋል።

የአድዋ ድል በቅኝ ግዛት ስር ለነበሩ ሁሉ የነጻነት መነሻ፤ ለተገፉ የሰው ልጆች ሁሉ ድል እንደሆነም ተናግረዋል።

“ለዚህ ወቅትም የአድዋ ድል ከአገር በላይ ምንም አለማስቀደምን ቡድናዊና ግላዊ ፍላጎት ሳይሆን አገራዊ ነገርን ማስቀደም እንደሚገባ አሳይቶናል” ብለዋል።

“ሁሉም ቂሙን ቁርሾውን ትቶ ለሚወዳት አገሩ በአንድነት በመውደቅ ለሚመጣው ትውልድ አገርን አስረክቧል” ያሉት ሚኒስትሯ፤ ከዚህ ተጨባጭ ገድል መማር እንደሚገባ አስገንዝበዋል።

“ይህ ትውልድ ከአገር በላይ ምንም እንደሌለ በሚገባ ማወቅ አለበት፣ ዘመን ተሻጋር ታሪክ መስራት አለበት ፍቅርና ወንድማማችነትን አንድነትን ከቀደሙት አባቶች መማር ይገባዋል” ብለዋል።

ይሕ ትውልድ የአገርን ሰንደቅ አላማ በልቦናው ጽፎ ደሃ የሚለውን ስም ለማጥፋት ሌት ተጠቀን መስራት እንዳለበት ገልጸው፤ “ከአድዋ ድል ትሩፋቶች ትምህርት ወስደን አገራችንን ወደ ብልጽግና እንምራት” ብለዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም