የአድዋ ድል ለኢትዮጵያዊያን ብቻ ሳይሆን ለመላው አፍሪካ የ'የይቻላል' ስነ-ልቦና ያጎናጸፈ ነው - አቶ ቱዋት ፓልቻይ

85

የካቲት 2013 (ኢዜአ) የአድዋ ድል ለኢትዮጵያዊያን ብቻ ሳይሆን ለመላው አፍሪካ የ'የይቻላል'ን ስነ-ልቦና ያጎናጸፈ ነው ሲሉ የኢትዮጵያ አንድነት አርበኞች ግንባር /ኢአአግ/ ሊቀ መንበር አቶ ቱዋት ፓልቻይ ገለጹ።

አቶ ቱዋት በህወሓት አገዛዝ የኢትዮጵያን ታሪክ በማደብዘዝ የጠላትን ተልዕኮ ለማሳካት ጥረት ሲደረግ ነበር ብለዋል።

በኤርትራና በሱዳን ጠረፋማ ቦታዎች ሸምቆ የትጥቅ ትግል ሲያካሂድ የቆየው የኢትዮጵያ አንድነት አርበኞች ግንባር አገራዊ ለውጡን ተከትሎ ሠላማዊ ትግል ለማድረግ ወደ ኢትዮጵያ መግባቱ ይታወቃል። 

የግንባሩ ሊቀመንበር ቱዋት ፓልቻይ 125ኛውን የአድዋ ድል በዓል አስመልክቶ ከኢዜአ ጋር ቆይታ አድርገዋል።

አቶ ቱዋት 'ኢትዮጵያ አንድነቷንና ሉዓላዊነቷን አስጠብቃ እስካሁን እንድትቆይ አድዋ ትልቅ መሰረት ጥሏል' ነው ያሉት።

ጀግኞች አርበኞች በኋላቀር መሳሪያ፣ በከፍተኛ ወኔና በአገር ፍቅር ስሜት ዘመናዊ መሳሪያ የታጠቀን ወታደር በማሸነፍ ዓለም የማይረሳው ደማቅ ታሪክ መጻፋቸውን አውስተዋል።

ይህ የድል ታሪክ ለኢትዮጵያዊያን ብቻ ሳይሆን ለመላው አፍሪካ የ'ይቻላል' ስነ-ልቦና ያጎናጸፈ መሆኑን ነው የተናገሩት።

ኢትዮጵያዊያን ምንም አይነት ችግር ቢኖርባቸው በአገር ሉዓላዊነት ጉዳይ ግን በጋራ ይቆማሉ ያሉት አቶ ቱዋት፤ ይህ ታሪክ ከትውልድ ትውልድ መተላለፍ ያለበት ቢሆንም የህወሓት አገዛዝ አደብዝዞታል ብለዋል።

ይህም የህወሓት አመራሮች የኢትዮጵያን መሰረታዊ ታረክ ከማደብዘዝ ባለፈ የጠላቶቿን ተልዕኮ ለማስፈጸም ሲሰሩ እንደነበር ማሳያ ነው ሲሉ አንስተዋል።

'የሃይል ትምክህት የትም እንደማያደርስ የአድዋ ድል ትልቅ ማሳያ ነው' ያሉት አቶ ቱዋት በተለይም ወጣቱ ትውልድ ታሪኩን በሚገባ በመረዳት አንድነቱን አስጠብቆ የተሻለች አገር የመገንባት ሃላፊነቱን እንዲወጣ ጠይቀዋል።

125ኛው የአድዋ ድል በዓል "አድዋ የኅብረ ብሔራዊ አንድነት አርማ" በሚል መሪ ሃሳብ ነው የሚከበረው።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም