በድባጤ ከተማ ከ470 ሺህ ብር በላይና የሞባይል ካርድ ይዘው ወደ ጋሊሳ ሊሄዱ የተዘጋጁ ሶስት ግለሰቦች በቁጥጥር ስር ዋሉ

79

አዲስ አበባ ጥር 21/2013 (ኢዜአ) በድባጤ ከተማ ሶስት ግለሰቦች ለጥፋት ቡድኑ የሚውል ከ470 ሺህ ብር በላይና የ26 ሺህ 680 ብር የሞባይል ካርድ ይዘው ወደ ጋሊሳ ሊሄዱ ሲሉ በኅብረተሰቡ ጥቆማ በቁጥጥር ስር መዋላቸውን የመተከል የተቀናጀ ግብረ ሃይል አስታወቀ።

ግለሰቦቹ ገንዘቡንና የ26 ሺህ 680 ብር የሞባይል ካርድ፣ አምስት ሲም ካርዶችና ሶስት የወታደራዊ መሳሪያ ማንገቻ ይዘው ወደ ጋሊሳ ሊሄዱ ሲሉ በቁጥጥር ስር የዋሉት በብሄራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎትና በኅብረተሰቡ ጥቆማ መሆኑ ተገልጿል።

ተጠርጣሪዎቹ ትናንት ጥር 20 ቀን 2013 ዓ.ም ከጠዋቱ 4 ሠዓት ከ30 አካባቢ ከቻግኒ ከተማ ወደ ድባጤ በሚሄድ የሕዝብ ማመላለሻ ተሽከርካሪ ላይ በቁጥጥር ስር ውለዋል።

የፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን የወንጀል መከላከል ዘርፍ ምክትል ኦፕሬሽን ሃላፊ ረዳት ኮሚሽነር ኢሳቅ አሊ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ተጠርጣሪዎቹ ወደ ጋሊሳ ቀበሌ በማቅናት ለጥፋት ቡድኑ ግብዓት ለማቅረብ ሲንቀሳቀሱ ነው በቁጥጥር ስር የዋሉት።

ከተጠርጣሪዎቹ አንደኛው በብሄራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት ክትትል ሲደረግበት እንደነበርና ቀሪዎቹ ገንዘቡን ሲቆጥሩ በኀብረተሰቡ ጥርጣሪ በጥቆማ የተያዙ መሆኑንም ገልፀዋል።

ከአንደኛው ተጠርጣሪ 368 ሺህ 40 ብር፣ ከሁለተኛው 76 ሺህ ብር፣ ከሶስተኛው ደግሞ የተለያየ መጠን ያላቸው የ26 ሺህ 680 ብር የሞባይል ካርድ በፍተሻ ተገኝቶባቸዋል ብለዋል።

ረዳት ኮሚሽነሩ ተጠርጣሪዎቹ በድባጤ ፖሊስ ጣቢያ ጉዳያቸው እየተጣራ መሆኑን ገልጸዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም