በልደታ ክፍለ ከተማ ስልጤ መስኪድ ጀርባ በፈነዳ ቦንብ የሰው ህይወት አለፈ

99

ታህሳስ 11/2013 (ኢዜአ) በአዲስ አበባ ከተማ ልደታ ክ/ከተማ ወረዳ 6 ልዩ ቦታው ስልጤ መስኪድ ጀርባ በፈነዳ ቦንብ የሰው ህይወት ማለፉን የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን አስታወቀ፡፡

ዛሬ ከጠዋቱ 2 ሰዓት ተኩል በልደታ ክፍለ ከተማ ወረዳ 6 ልዩ ቦታው ስልጤ መስኪድ ጀርባ ለልማት በፈረሰ ክፍት ቦታ ላይ ማንነታቸው ባልታወቁ ግለሰቦች ተጥሎ በተገኘ የእጅ ቦንብ ጎዳና ተዳዳሪ የሆኑ የሦስት ሰዎች ህይወት ሲያልፍ በአምስት ሰዎች ላይ ቀላልና ከባድ የአካል ጉዳት መድረሱን ኮሚሽኑ ገልጿል።

በኮሚሽኑ የልዩ ልዩና የተደራጁ ወንጀሎች ምርመራ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ኮማንደር አለማየሁ አያልቄ ከፍንዳታው ጋር በተያያዘ ያለው የምርመራ ሂደት እየተጣራ መሆኑን ገልፀው፤ የምርመራ ውጤቱ እንደተጠናቀቀ ለህብረተሰቡ ግልጽ ይደረጋል ነው ያሉት።

በተለያዩ ቦታዎች እንደ አልባሌ በሚጣሉ ቦንቦችና ፈንጂዎች ንፁሀን ሰለባ መሆናቸውን ያስታወሱት ዳይሬክተሩ፤ ህብረተሰቡ ምንነታቸው ያልታወቁ አጠራጣሪ ነገሮች ሲያጋጥሙት ከመነካካት በመቆጠብ ለሚመለከታቸው የፀጥታ አካላት ጥቆማ ማድረግ እንደሚገባ መልዕክት ማስተላለፋቸውን ከአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ያገኘነው መረጃ ያሳያል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም