የሆቴልና ቱሪዝም ማሰልጠኛ ማዕከል ለመከላከያ ሰራዊት እና ለአገራዊ ፕሮጀክቶች የ2 ነጥብ 5 ሚሊዮን ብር ድጋፍ አደረገ

63

አዲስ አበባ ህዳር 18/2013 (ኢዜአ) የሆቴልና ቱሪዝም ማሰልጠኛ ማዕከል ለአገር መከላከያ ሰራዊትና ለሁለት አገራዊ ፕሮጀክቶች ማስፈጸሚያ የ2 ነጥብ 5 ሚሊየን ብር ድጋፍ አደረገ።

ተቋሙ በሕግን ማስከበር ዘመቻ ለተሰማራው የአገር መከላከያ ሰራዊት አንድ ሚሊዮን ብር ድጋፍ ያደረገ ሲሆን፤ ለታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ የአንድ ሚሊዮን ብር እንዲሁም ለ"ገበታ ለሀገር" ፕሮጀክት ማስፈጸሚያ ግማሽ ሚሊዮን ብር አበርክቷል።

የባህልና ቱሪዝም ሚኒስትሯ ዶክተር ሂሩት ካሳው “ድጋፉ ሰራዊቱ የሚያካሂደውን የሕግ ማስከበር ዘመቻ በመደገፍ አገራዊ የልማት ፕሮጀክቶችን ማስቀጠል እንደሚቻል ለማሳየት ነው" ብለዋል።

ተቋማት ለአገር መከላከያ ሰራዊት ከሚያደርጉት ድጋፍ በተጓዳኝ አገራዊ የልማት ፕሮጀክቶችን ለማስቀጠል ድርሻቸውን እንዲወጡም መልዕክት አስተላልፈዋል።

የሆቴልና ቱሪዝም ማሰልጠኛ ማዕከል ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ ገዛኸኝ አባተ ድጋፉ ሰራዊቱ እያደረገ ያለውን የሕግ ማስከበር ሥራ ለመደገፍና አገራዊ የልማት ፕሮጀክቶችን ለማስቀጠል ድጋፉ መደረጉን ተናግረዋል።

የአገር መከላከያ ሚኒስትር ዴኤታ ወይዘሮ ማርታ ሉዊጂ ለተደረገው ድጋፍ ምስጋና አቅርበው፤ “የተደረገው ድጋፍ ለሰራዊቱ ትልቅ ሞራላዊና ቁሳዊ እገዛ ያደርጋል” ብለዋል።

የታላቁ ኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ ሕዝባዊ ተሳትፎ ማስተባበሪያ ብሔራዊ ምክር ቤት ጽህፈት ቤት ዋና ዳይሬክተር ዶክተር አረጋዊ በርሄ በበኩላቸው ተቋሙ ለሰላም ማስከበርና ለአገራዊ ፕሮጀክቶች ላደረገው ድጋፍ ምስጋና አቅርበዋል።

ኢትዮጵያውያን ሕግን ለማስከበር ለሚዋደቀው ሰራዊትና ለግድቡ የሚያደርጉትን ድጋፍ እንዲያጠናክሩም ጠይቀዋል።

ለግድቡ ግንባታ የሚደረገው ሕዝባዊ ተሳትፎ መጠናከሩም በሥነ ሥርዓቱ ላይ ተገልጿል።

በአገር አቀፍ ደረጃ በ"ገበታ ለሀገር" ለተያዙት የጎርጎራ፣ ኮይሻና ወንጪ ፕሮጀክቶች የሚደረገው ተሳትፎ እንዲጎለብትም ጥሪ ቀርቧል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም