ዶክተር ፍቅሬ ማሩን ጨምሮ የ62 ተካሳሾች ክስ እንዲነሳ ተወሰነ

57
አዲስ አበባ ግንቦት 3/2010 የፌደራል ጠቅላይ አቃቤ ህግ ዶክተር ፍቅሬ ማሩን ጨምሮ የ62 ተከሳሾችን የክስ ሂደት ማንሳቱን አስታወቀ። ተከሳሾቹ የወንጀለኛ መቅጫ ህግን አንቀጽ 464 እና 494 በመተላለፍ ጉዳያቸው በፍርድ ሂደት ላይ ያለና እንዲከላከሉ ብይን የተሰጠባቸው ናቸው። ኢዜአ ከፌደራል ጠቅላይ አቃቤ ህግ ባገኘው መረጃ መሰረት በእነ አበበ የኋላ መዝገብ የተጠቀሰውን አንቀጽ በመተላለፍ ጉዳያቸው በፍርድ ሂደት ላይ ያለ 18 ተከሳሾች ክስ እንዲነሳ ተወስኗል። በእነ ማስረሻ ሰጠኝ መዝገብ በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 19ኛ ምድብ ችሎት ጉዳያቸው ሲታይ ከነበሩት 38 ተከሳሾች መካከል አራቱ በሰው መግደል ወንጀል ክስ ቀርቦባቸው እንዲከላከሉ ብይን የተሰጠ ሲሆን፤ ስምንቱ ደግሞ በነጻ መሰናበታቸው ይታወቃል። በተጠቀሰው መዝገብ የወንጀለኛ ህጉን አንቀጽ 464 እና 494 በመተላለፍ እንዲከላከሉ ብይን የሰጠባቸውን ቀሪ 26 ተከሳሾች ክስ እንዲነሳ ሲወሰን፤ በሰው መግደል ወንጀል እንዲከላከሉ የተበየነባቸው የአራቱ ተከሳሾች የፍርድ ሂደት ግን ባለበት ይቀጥላል ተብሏል። በተመሳሳይ በእነ ቴዎድሮስ ዳንኤል መዝገብ የወንጀለኛ ህጉን አንቀጽ 464 እና 494 በመተላለፍ ጉዳያቸው በፍርድ ሂደት ላይ ያለ የ18 ተከሳሾች ክስ  እንዲነሳ መወሰኑን የፌዴራል ጠቅላይ አቃቤ ህግ አስታውቋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም