በአዲስ አበባ ከተማ ለኢሬቻ በዓል የሚዘጉ መንገዶችን ፖሊስ ይፋ አደረገ

211

አዲስ አበባ፣ መስከረም 21/2013 ( ኢዜአ)  በአዲስ አበባ ከተማ ለኢሬቻ በዓል ከዋዜማው ጀምሮ ለተሽከርካሪዎችና ለእግረኞች ዝግ የሚሆኑ መንገዶችን የከተማ አስተዳደሩ ፖሊስ ይፋ አድርጓል፡፡

በዓሉ በሰላም እንዲከበር የፀጥታ አካላት ዝግጅታቸውን ማጠናቀቃቸውንም አስታውቋል፡፡

በከተማው ነገ ከቀኑ 10 ሰዓት 30 ጀምሮ የሚዘጉት መንገዶች የሚከተሉት ናቸው፦

ከቦሌ አየር መንገድ ፣በሚሌኒየም አዳራሽ ወደ መስቀል አደባባይ የሚወስደው መንገድ ደምበል ሲቲ ሴንተር ኦሎምፒያ አደባባይ፡፡

ከመስቀል ፍላወር ወደ ኦሎምፒያ የሚወስደው መንገድ ማዘጋጃ ጋራዥ ወይም ጋዜቦ አደባባይ፡፡

ከመገናኛ ፣በሃያ ሁለት ወደ መስቀል አደባባይ እንዲሁም ከቦሌ መድኃኔዓለም ፣በአትላስ ሆቴል ወደ መስቀል አደባባይ የሚወስደው መንገድ ቅዱስ ዑራኤል ቤተ-ክርስቲያን አካባቢ፡፡

ከፒያሳ ወደ መስቀል አደባባይ የሚወስደው መንገድ ቴዎድሮስ አደባባይ፡፡

ከአራት ኪሎ ወደ መስቀል አደባባይ የሚወስደው መንገድ ባሻ ወልዴ ችሎት ወይም ፓርላማ መብራት ላይ ዝግ ይሆናል፡፡

እንዲሁም ከሳሪስ ፣በጎተራ ወደ መስቀል የሚወስደው መንገድ አጎና ሲኒማ፡፡

ከካዛንቺስ በቤተ መንግስት ፍል ውሃ የሚወስደው መንገድ ኢንተር ኮንቲኔንታል ሆቴል ፣ከዑራኤልና አዋሬ የሚመጡ መንገዶች ካዛንቺስ ቶታል ላይ ይዘጋሉ፡፡

በተጨማሪም ከካዛንቺስ ወደ አራት ኪሎ የሚወስደው መንገድ ግቢ ገብርኤል መስቀለኛው ላይ፡፡

ከተክለሃይማኖት ፣በሚቲዎሮሎጂ ፣መስቀል አደባባይ የሚወስደው መንገድ ሚቲዎሮሎጂ መስሪያ ቤት አካባቢ ይዘጋል፡፡

ከተክለሃይማኖት፣ በጥቁር አንበሳ ሆስፒታል፣ ኢሚግሬሽን ጥቁር አንበሳ የኋላ በር መስቀለኛው ላይ፡፡

ከጌጃ ሰፈር፣ ጤና ጥበቃ፣ ብሄራዊ ቲያትር የሚወስደው መንገድ ጎማ ቁጠባ የትራፊክ መብራት፡፡

ከቄራ ወደ ቂርቆስ የሚወስደው መንገድ ታቦት ማደሪያ፡፡

ከጦር ኃይሎች ፣ልደታ ፣ከፖሊስ ሆስፒታል ሜክሲኮ አደባባይ ያለው መንገድ ዝግ ይሆናሉ፡፡

በዓሉ በሚከበርበት ዙሪያና አካባቢው ነገ  ከቀኑ 8 ሰዓት 30 ጀምሮ ፕሮግራሙ እስኪጠናቀቀ ድረስ በግራና በቀኝ ለረጅምም ሆነ ለአጭር ጊዜ ተሽከርካሪ አቁሞ መሄድ በፍጹም የተከለከለ መሆኑን ኮሚሽኑ ገልጿል፡፡

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም