የወንጀል ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ሥር የሚውሉት ድርጊታቸው ተጣርቶ ነው - የፌዴራል ጠቅላይ ዐቃቤ ህግ

109

አዲስ አበባ፣ መስከረም 20/2013(ኢዜአ) በርካታ የወንጀል ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ሥር የሚውሉት የፈፀሙት ድርጊት ከተጣራ በኋላ መሆኑን የፌዴራል ጠቅላይ ዐቃቤ ህግ ገለጸ።

በሀገሪቱ ከ2013 እስከ 2022 ለአስር ዓመታት የሚተገበረውን የተቋሙን ስትራቴጂክ እቅድ በተመለከተ ከክልል የጠቅላይ ዐቃቤ ህግ ተቋማት ጋር ውይይት ተደርጓል።

የፌዴራል ምክትል ጠቅላይ ዐቃቤ ህግ አቶ ገለታ ስዩም፤ ኢትዮጵያ በ2022 ዓ.ም የአፍሪካ የፍትህ ተቋማት ተምሳሌት እንዲትሆን ለማስቻል እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል።

የህዝብን አመኔታ ያተረፈ የፍትህ ሥርዓት እውን ለማድረግ ትልልቅ አገራዊ የወንጀል ጉዳዮች ላይ ተሳትፎ ያላቸው አካላት ተጠያቂ እየሆኑ ነው ብለዋል።

ከዚህም ባለፈ ማንኛውንም በወንጀል የተጠረጠሩ በቁጥጥር ሥር እየዋሉና በበቂ ምርመራ ታግዞ ተጠያቂ አንዲሆኑ እየተደረገ መሆኑን ጠቅሰዋል።

የምርመራ ሂደቱ ተጣርቶ ማስረጃ እስኪቀርብ ሊጠፉ ይችላሉ ተብለው የሚጠረጠሩ ግን ቀድመው በቁጥጥር ስር እንዲውሉ ይደረጋል ነው ያሉት።

አሁን ላይ ወንጀለኞች በፈጸሙት ድርጊት ልክ ተገቢውን ቅጣት እንዲያገኙ የማድረግ ምጣኔ ከ56 ወደ 91 በመቶ ከፍ ማለቱንም ገልጸዋል። 

ወንጀልን የመከላከል ሃላፊነት በዋነኝነት የመንግስት ሃላፊነት ቢሆንም የሁሉም ዜጋ ተሳትፎና እገዛ ወሳኝ መሆኑን አቶ ገለታ ገልጸዋል።

ወንጀልን በመከላከል የመንግስትና የህዝብን ጥቅም ማስጠበቅ ብሎም የህዝብን አመኔታ ያተረፈ የፍትህ ሥርዓት ማስፈን የቀጣይ ሥራችን የሆናልም ነው ያሉት።

ለዚህ ደግሞ የማኅበረተሰቡን የህግ ግንዛቤ ማሳደግ ዋና ትኩረት መሆን ይኖርበታል ብለዋል።

የቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል ምክትል ጠቅላይ ዐቃቤ ህግ አቶ ንጋቱ አለሙ እና የኦሮሚያ ክልል ምክትል ጠቅላይ ዐቃቤ ህግ አቶ ታደሰ ንጉሴ ተቋማት በህግ ጉዳይ ያስተማሩትን የሰው ብዛት ያክል ለማብቃት አልሰሩም ብለዋል።

በመሆኑም ዜጎች መብትና ግዴታቸውን አውቀው ራሳቸውን ከወንጀል ድርጊት እንዲያርቁ ወንጀለኞችን ለህግ አሳልፈው እንዲሰጡ በህግና ፍትህ ላይ በቂ ግንዛቤ መፍጠር ይኖርብናል ነው ያሉት።

የፌዴራል ምክትል ጠቅላይ ዐቃቤ ህግ አቶ ገለታ እንደሚሉት ወንጀለኞችን ለህግ የማቅረብ ተግባር እንዳለ ሆኖ አስተዳደራዊ መፍትሄዎችም ተጠናክረው መቀጠል አለባቸው።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም